1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

ወደ ሰላም ተመለሱ የተባሉት የኦነግ-ኦነሰ ታጣቂዎች ጉዳይ

ሥዩም ጌቱ
ሰኞ፣ ታኅሣሥ 13 2018

በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ወለጋ ዞን በተለያዩ ወረዳዎች ስንቀሳቀሱ ነበሩ የተባሉ ከ200 በላይ ታጣቂዎች ወደ ሰላም መመለሳቸውን መንግስት አስታውቋል፡፡ ከቀናት በፊትም በተመሳሳይ በጉጂ ዞን ታጣቂዎቹ በገፍ ትጥቅ አስረክበው ወደ ሰላም መመለሳቸው ተነግሮ ነበር፡፡ በመንግስት ምህረት የተመለሱት ታጣቂዎችን ጉዳይ በአሉታዊ የሚመለከቱ ጥቂቶች አይጠፉም፡፡

Äthiopien Oromia | Teile der Region Oromia
ምስል፦ Seyoum Getu/DW

ወደ ሰላም ተመለሱ የተባሉት የኦነግ-ኦነሰ ታጣቂዎች ጉዳይ

This browser does not support the audio element.

“የኦነግ-ኦነሰ ታጣቂዎች ወደ ሰላም ተመለሱ” መባል፤ የሕዝብ አስተያየት

ከትናንት በስቲያ ቅዳሜ ታህሳስ 11 ቀን 2018 ዓ.ም. በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ወለጋ ዞን በተለያዩ ወረዳዎች ስንቀሳቀሱ ነበሩ የተባሉ ከ200 በላይ ታጣቂዎች ወደ ሰላም መመለሳቸውን መንግስት አስታውቋል፡፡ ከቀናት በፊትም በተመሳሳይ በጉጂ ዞን ታጣቂዎቹ በገፍ ትጥቅ አስረክበው ወደ ሰላም መመለሳቸው ተነግሮ ነበር፡፡ በዚህ ላይ አስተያየታቸውን የሰጡ የያከባቢዎቹ ነዋሪዎች ይህ የታጣቂዎች ወደ ሰላም መመለስ ብያንስ ጊዜያዊ እፎይታ እያመጣ ነው ባይ ናቸው፡፡

ከትናንት በስቲያ ቅዳሜ በኦሮሚያ ክልል ታጣቂዎች በስፋት ከምንቀሳቀሱባቸው አከባቢዎች አንዱ በሆነው ምዕራብ ኦሮሚያ ምስራቅ ወለጋ ዞን 200 የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት ታጣቂዎች ትጥቃቸውን ለመንግስት አስረክበው ወደ ሰላማዊ የፖለቲካ አማራጭ መመለሳቸውን ነው መንግስት ያስታወቀው፡፡ ለምንግስት ቅርበት ያላቸው መገናኛ ብዙሃን እንደዘገቡት በዞኑ ጊዳ አያና፣ ኪረሙ፣ ኤባንቱ እና ሊሙ ወረዳዎች ታጣቂዎቹ ከነሙሉ ትጥቃቸው ወደ ሰላም ሲመለሱ በአከባቢው ማህበረሰብ እና በመንግስት ባለስልጣናት አቀባበል እንደተደረገላቸውም ተሰምቷል፡፡

ግጭት ውስጥ በቆየው ኪረሙ የሰላም ተስፋ

ታጣቂዎቹ በስፋት መመለሳቸውን በማረጋገጥ አስተያየታቸውን ለዶይቼ ቬለ የሰጡ የምስራቅ ወለጋ ዞን ኪረሙ ወረዳ ነዋሪ፤ “አንድም ሁለትም እያሉ ስመለሱ ለህዝቡ ትልቅ እረፍት ነው የሚሰጠው” በማለት በዚህ ባለፉት ዓመታት በተፈየጠረው ግጭት የደረሱ የኢኮኖሚ እና ማህበራዊ ቀውስ ጠባሳዎች ከቤተሰብ መበታተን እስከ የሰው ህይወት መጥፋት ያደረሰ ሰፋፊ ኪሳራ ሲሉ አብራርተዋል፡፡ የህዝቡ መሰረታዊ ፍላጎት ሰላም ነው የሚሉት አስተያየት ሰጪው ነዋሪ በአከባቢው ተፈጥሮ በቆየው ግጭት እስከ ስድስት ዓመታት ለዘለቀ ጊዜ ቤተሰብ ከቤተሰብ ተለያይቶ በደስታና ሃዘን መሳተፍን ከባድ አድርጎትም እንደቆየ ገልጸዋል፡፡

አስተያየት ሰጪው በአስተያየታቸው እንዳከሉት ግን የታጣቂዎችን በመንግስት ምህረት መመለስ በአሉታዊ የሚመለከቱ ጥቂት የማህበረሰብ አካላትም አይጠፉም፡፡ “ቤተሰቦቻቸው የተጎዳባቸው ሰዎች አሁን ታጣቂዎቹ በሰላም ገብተው ማህበረሰቡን ስቀላቀሉ አሉታዊ በሆነ መንገድ ያያሉ” በማለት ይህም ለጉዳታቸው ተመጣጣኝ ፍትህ የአለማግኘት ስሜት ስለሚፈጥርባቸው እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ በዚህ ለዓመታት ሰላምና መረጋጋት በራቀው ወረዳቸው “የፋኖ ታጣቂዎችም” መኖራቸውን የገለጹት አስተያየት ሰጪው ነዋሪ ሁሉም አይነት ታጣቂዎች ወደ ሰላም የሚመለሱ ከሆነ ሰላምና መረጋጋቱ ሙሉ ሊሆን ስለሚችል ያ ሲሆን ማህበረሰቡ አምርቶ መኖር እንዲችልም በሙሉ አፍ ለመግለጽ እንደሚያስችልም በአስተያየታቸው አመልክተዋል፡፡ ለዚህም የመንግስት የፀጥታው ጥበቃ እንዲሰፋ ጠይቀዋል፡፡

በምዕራብ ጉጂ መጥቷል የተባለው መሻሻል

ኦሮሚያ ክልል ታጣቂዎች በስፋት ትጥቃቸውን በማስቀመጥ ወደ ሰላማዊ የፖለቲካ መንገድ መመለሳቸው በተነገረበት በምዕራብ ጉጂ ዞን እስከ መስከረም ወር አጋማሽ ላይ 114 ታጣቂዎች ትጥቅ ማስቀመጣቸውን እንዲሁም በዚህ ዓመት በዞኑ ብቻ 500 ያህል ታጣቂዎች ከጫካ መመለሳቸውን የአከባቢው ባለስልጣናት ይናገራሉ፡፡ ይህንኑን አረጋግጠው አስተያየታቸውን የሰጡን አንድ የዞኑ ቡሌሆራ ወረዳ ነዋሪ፤ “ከሰላሙ አኳያ አሁን ለውጥ መጥቷል፡፡ በርካታ ታጣቂዎችም በሂደት ወደ ሰላም ተመልሰው እየገቡ ስለሆነ መረጋጋት አለ፡፡ እንደውም በዚህ አከባቢ አልፎ አልፎ ከሶማሊ ክልል አዋሳኝ አከባቢ ካለው አልፎ አልፎ ከሚስተዋል ግጭት ውጪ አሁን የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት ታጣቂዎች በመግባታቸው መረጋጋት ተፈጥሯል” ብለዋል፡፡

ፎቶ ከማኅደር፤ የታጣቂዎች ሰላማዊ ሶችን ላይ የሚፈፅሙትን ግድያ የተቃወመ ሰላማዊ ሰልፍ በበርሊን ምስል፦ Tirsit Trimborn

የባለስልጣናት አስተያየት

ከሁለት ወራት በፊት በመስከረም ወር አጋማሽ በሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ዞን ጃርደጋ ጃርቴ ወረዳ እና ሻምቡ ዙሪያ እንዲሁ ታጣቂዎች በገፍ ትጥቅ ፈተው ወደ ሰላም ተመልሰዋል መባሉን ተከትሎ አስተያየታቸውን ለዶይቼ ቬለ የሰጡት የኦሮሚያ ክልል ኮሚዩኒኬሽን ኃላፊ አቶ ኃይሉ አዱኛ፤ መሰል ሂደቶች ግጭትን እየቀነሱ ሰላምን በዘላቂነት ለማጽናት ጉልህ አስተዋጽኦ ይኖራቸዋል ብለዋል፡፡ በዚህ ላይ በወቅቱ ተጠይቀው ስተያየታቸውን የሰጡን የኦነግ-ኦነሰ ከፍተኛ አዛዥ አማካሪ አቶ ጅሬኛ ጉደታ፤ ግን ሂደቱን በመንቀፍ “ፕሮፓጋንዳ” ማለታቸው አይዘነጋም፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት ከዚህ በፊት በሁለት ዙር ከኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት (ኦነሰ) ጋር በታንዛንያ ሰላም ለማውረድ ያደረገው ጥረት ፍሬ ሳያፈራ ያለስምምነት መቋጨቱ አይዘነጋም፡፡

ሥዩም ጌቱ

አዜብ ታደሰ

ኂሩት መለሰ

ቀጣዩን ክፍል እለፈው የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል እለፈው ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW