ዌስት ባንክ ውስጥ በ DW ሰራተኞች ላይ ለደረሰዉ ጥቃት ትችት ቀረበ
ሰኞ፣ ሰኔ 30 2017
በዌስት ባንክ ውስጥ በDW ሰራተኞች ለደረሰዉ ጥቃት ትችት ቀረበ
በሁለት የዶይቸ ቬለ (DW) ጋዜጠኞች ላይ በምዕራብ ዮርዳኖስ ዳርቻ ላይ የሰፈሩ እስራኤላዉያን ጥቃት ካደረሱ በኋላ የጀርመን ጋዜጠኞች ማህበር በጉዳዩ ላይ ማብራርያ ጠየቀ። ከዚህ ቀደም ሲል በእስራኤል የሚገኙት የጀርመን አምባሳደር ድርጊቱን አዉግዘዉታል።
የጀርመን ጋዜጠኞች ማህበር (DJV) በዌስት ባንክ የሰፈሩ እስራኤላዉን በዶይቸ ቬለ ጋዜጠኞች ላይ ጥቃት ማድረሳቸዉን ተከትሎ ስጋቱን ገልጿል። የማኅበሩ ሊቀመንበር ሚካ ቢስተር "አክራሪ ሰፋሪዎች የሚዲያ ሰራተኞችን ያለምንም ቅጣት እያደኑ መቀጠል አይችሉም። ይህ ያለምንም እርምጃ መተዉ የለበትም» ሲሉ ትናንት እሁድ ተናግረዋል።
የእስራኤል መንግስት ጥቃቱን መርምሮ ለህግ የማቅረብ ግዴታ አለበት። ጥቃቱ እንደሚያሳየው በክልሉ ውስጥ የሚገኙ ጋዜጠኞችን ደህንነት ለመጠበቅ በጣም ትንሽ ነገር መደረጉን ነዉ፤ ሲሉም የማህበሩ ሊቀመንበር አክለዋል።
ዓለም አቀፍ የመገናኛ ብዙኃን ስርጭት አቅራቢው ዶይቸ ቬለ ባለፈዉ ቅዳሜ ቦን ከሚገኘዉ ዋና መሥርያ ቤት እንዳስታወቀዉ እየሩሳሌም የሚገኘው የ DW ፅህፈት ቤት ዘጋቢ እና የካሜራ ባለሙያ በድንጋይ ጥቃት ደርሶባቸዋል፤ ተሳደዋል። ይሁንና ሁለቱም የዶይቸ ቬለ ባልደረቦች ምንም ጉዳት ሳይደርስባቸዉ ማምለጥ ችለዋል ተብሏል። የካሜራ ባለሙያው ተሽከርካሪ ግን ከፍተኛ ጉዳት ደርሶበታል።
እንደ DW ዘገባ ከሆነ ድርጊቱ የተፈፀመው ባለፈዉ አርብ ዕለት በሲንጂል መንደር በፍልስጤም በሚተዳደረው በእስራኤል ይዞታ ስር በሚገኘው በምዕራብ ዮርዳኖስ ዳርቻ ዉስጥ ነው። ከ DW በተጨማሪ ሌሎች የዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃኖች ጉዳዩን ለመዘገብ በቦታው እንደነበሩም ተዘግቧል፤ ከተገኙት ዓለም አአፍ ሚዲያዎች መካከል የፈረንሳዩ የዜና አገልግሎት አዣንስ ፍራንስ ፕሬስን ጨምሮ "ኒውዮርክ ታይምስ" እና "ዋሽንግተን ፖስት" ይገኙበታል። የDW የሚዲያ ሰራተኞች በፕሬስ ልብሳቸው በግልፅ ይታወቃሉ። የእስራኤል መንግስት በጉዳዩ ላይ እስካሁን የሰጠው መግለጫ የለም።
የ DW ዳይሬክተር ለእስራኤል መንግስት ጥሪ አቅርበዋል
የDW የመገናኛ ብዙኃን ማሰራጫ ጣብያ ዋና ዳይሬክተር ፒተር ሊምቡርግ "DW ወደ ሲንጂል ተጉዘዉ የሰፋሪዎችን ጥቃት ተቃውሞን ለመዘገብ በመጡ ባልደረቦቻችን ላይ የደረሰውን ጥቃት ያወግዛል" ብለዋል። የእስራኤል መንግስት በዌስት ባንክ የሚገኙ ጋዜጠኞችን ደህንነት እንዲያረጋግጥ ተማጽነዋልም። "የፕሬስ ነፃነት እና የጋዜጠኞችን ደህንነት የየትኛውም ዲሞክራሲ አስፈላጊ ምሰሶ ነው" ሲሉም አጽንዖት ሰጥተዋል።
በእስራኤል የጀርመን አምባሳደር ስቴፈን ሴይበርት በበኩላቸዉ በዓለም አቀፍ ጋዜጠኞች ላይ ሰፋሪዎች የሚያደርሱት የኃይል እርምጃ እጅግ አሳሳቢ ናቸው፤ “የፕሬስ ነፃነት እና የጋዜጠኞች ደህንነት መረጋገጥ ይኖርበታል፤ ሲሉ በኤምባሲዉ X ገጽ ላይ መልክታቸዉን አስተላልፈዋል።
አዜብ ታደሰ
እሸቴ በቀለ