የኢትዮጵያ መንግስት መምህራንን እያወያየ ነው
ረቡዕ፣ መስከረም 11 2009ማስታወቂያ
ዘላቂ መፍትሔ ባያገኝም ለጊዜው ቀዝቀዝ ባለው ተቃውሞ ማግስት የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን ጨምሮ በመላ አገሪቱ መምህራንን እና በትምህርት አስተዳደር ዘርፍ የሚገኙ ሰራተኞችን ሲያወያዩ ቀናት ተቆጠሩ። ውይይቱ በትምህርት አገልግሎቱ ላይ ቢያተኩርም ለመምህራኑ ግን አዲስ አይደለም። በአምቦ ዩኒቨርሲቲ መምህር የሆኑት አቶ ስዩም ተሾመ ለውይይት የቀረበው ርዕሰ ጉዳይ ካለው ነባራዊ ሁኔታ ጋር የማይገናኝ እንደሆነ ይናገራሉ።
ማንነታቸውን ሊነግሩን ያልፈለጉ ሌላ መምህር አንድ ከፍተኛ ባለስልጣን በመሩት ውይይት ላይ ተሳትፈዋል። መምህሩ በዛሬው ውሏቸው የታደሙበት ጉባኤ ከሌላው ጊዜ የተለየ እንዳልነበር ይናገራሉ።
የኢትዮጵያ መንግስት ለውይይት ባቀረባቸው ሰነዶች ወቅታዊ የአገሪቱ ነባራዊ ሁኔታዎች እንዳልተካተቱበት መምህራኑ ተናግረዋል። ለውይይት የቀረቡት ሰነዶች ካለፉት ዓመታት የተለየ አንዳች ነገር የለውም ሲሉ ይተቻሉ። የውይይት ሰነዶቹ ላይ የቀረቡት ስኬቶችም በገዢው ፓርቲ አይን ብቻ መቅረባቸው በመምህራኑ ዘንድ ጥያቄ አስነስቷል። በአንዳንድ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት መምህራኑ በዝምታ ተቃውሟቸውን ማሳየታቸውንም ተናግረዋል።
በአማራ እና ኦሮሚያ ክልሎች ተቃውሞ ስትናጥ የከረመችው ኢትዮጵያ የ2009 ዓ.ም. የትምህርት ዘመንን ልትጀምር በዝግጅት ላይ ትገኛለች። ወትሮም ለተቃውሞ መነሻ በመሆን የሚታወቁት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በአዲሱ የትምህርት ዘመን ሥጋት መፍጠራቸው አይቀርም። አቶ ስዩም አሁን በተፈጠሩት ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ጥልቅ ውይይት መደረግ እንደነበረበት ይናገራሉ።
እሸቴ በቀለ
ሒሩት መለሰ