ውይይት፦ ምን ያስተሳስረው ይሆን? ግጭት ኢትዮጵያ እና ጎረቤት አገራት
እሑድ፣ ኅዳር 14 2018
ምሥራቅ አፍሪቃን ጦርነት እና ውጥረት ሰቅዞ ከያዘ ሰነባብቷል ። ሰሜን ኢትዮጵያ የትግራዩ ጦርነት በሚል የሚታወቀው ውጊያ ትግራይ፤ አማራ እና አፋር ክልሎችን አድቅቆ፤ የበርካቶችን ሕይወት ገብሮ አልፏል ። በዚያ ግን አላባቃም ። የፕሪቶሪያው የተኩስ ማቆም ስምምነት በኢትዮጵያ መንግሥት እና በሕወሓት መካከል ከተደረገ በኋላ በስምምነቱ እንድንሳተፍ አልተደረግንም የሚሉ ቅሬታዎች ከየአቅጣጫው አስተጋብተዋል ።
የኢትዮጵያ መንግሥትን ደግፎ በትግራይ ክልል ጦር ያዘመተው የኤርትራ መንግሥት ያኔ ከደገፈው ኃይል ጋር አሁን ዐይን እና ናጫ ከመሆንም አልፈው መፋጠጣቸው ይዘገባል ።
በአማራ ክልል የፋኖ ታጣቂዎች ከመንግሥት ጦር እና ተባባሪዎቹ ጋር መፋለም መጀመራቸው ከተነገረ ዓመታት ተቆጥሯል ። አማራ ክልልን በስፋት በምትዋሰነው ሱዳን የጦር ኃይሏ እና ፈጥኖ ደራሽ ኃይሉ ውጊያ ከገቡ እዚያም ዓመታት ተቋጥሯል ። የሱዳን ጦርን እና ዋነኛ ባላናንጣው የፈጥኖ ደራሹን ኃይል የሚደግፉ የባሕረ ሠላጤው አገራት የኢትዮጵያ መንግሥትን እና የኤርትራ መንግሥትን በየፊናቸው እንደሚደግፉ ይነገራል ።
ኢትዮጵያ ውስጥ የሚከሰተው ግጭት ሱዳን ውስጥ፥ የሱዳኑ ኢትዮጵያ ውስጥ ነጸብራቁ በጉልኅ ይታያል ። ከፍ ሲል ግብጽ ከወደታች ደግሞ ሶማሊያም በግጭት ውጥረቱ ስማቸው በተደጋጋሚ ይነሳል ። የምሥራቅ አፍሪቃው ግጭት እና ውጥረት በአገራቱ ላይ ያስከተለውን ሰብአዊ ቀውስ፣ ፖለቲካዊ ውጥረት እና ኤኮኖሚያዊ ተግዳሮት በዛሬው ውይይት ለመዳሰስ እንሞክራለን ።
በውይይቱ 4 እንግዶች ተሳታፊ ሆነዋል፦
-
አቶ ባይሳ ዋቅ ወያ፤ የዓለም አቀፍ ሕግ ባለሞያ እና የቀድሞዉ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዲፕሎማት
-
አቶ አብድራህማን ሠይድ፤ የአፍሪቃ ቀንድ ፖለቲካ ተንታኝ
-
አቶ መስፍን አማን የፖለቲካ ተንታኝ ብሎም ተማሪ
-
አቶ ያሬድ ኃይለማሪያም፤ የህግ ባለሞያ እና የሰብአዊ መብት ተሟጋች በአሁኑ ወቅት አማካሪ ናቸው ።
የውይይቱ ተሳታፊዎች በኢትዮጵያ እና በጎረቤት አገራት መካከል ስላለው ወቅታዊ ግጭት እና የፖለቲካ ውጥረት በማብራራት ይጀምራሉ ። ኢትዮጵያን ጨምሮ በጎረቤት አገራቱ መካከል ያለውን ግጭት እና ፖለቲካዊ ውጥረት የሚያያይዘው ነገር የሚሉትንም ይተነትናሉ ። በምሥራቅ አፍሪቃ ፖለቲካዊ ውጥረት እና ግጭት ረዣዥም እጆቻቸውን ስለዘረጉ አገራት በማንሳት በዋናነት እነማን እንደሆኑም ይጠቅሳሉ ። የባለረዣዥሞቹ አገራት ተጽእኖ ጥልቀት እና ስፋቱ ይዳሰሳል ። በስተመጨረሻም በቀጣናው የቀጠለው ጦርነት ተባብሶ መልኩን በመቀየር ተጨማሪ እልቂት ብሎም ብርቱ ሰብአዊ ቀውስ እንዳያስከትል መደረግ አለበት የሚሉትንም ተወያዮች ያካፍላሉ ።
ሙሉውን ውይይት በድምፅ ማእቀፉ በኩል ማድመጥ ይቻላል ።
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ነጋሽ መሐመድ