ዚምባብዌ እና የገጠማት የምግብ እጥረት
ሰኞ፣ ጥር 13 2005 በዓለም መንግሥታቱ ድርጅት ዘገባ መሠረት፡ የምግቡ እጥረት ችግር የተከሰተው ብርቱ ዝናብ ሰብሉን በማበላሸቱ፡ የግብርና መሣሪያዎች እና ዘመናዩ የግብርና አሰራር በመጓደሉ ነው።
በዚምባብዌ የሚታየው የሰብዓዊ ቀውስ ምንም እንኳን ካለፉት ጥቂት ዓመታት ወዲህ ጥቂት መሻሻል ቢያሳይም፡ ሁኔታው አሁንም አሳሳቢ መሆኑን የርዳታውን ጥሪ ያስተላለፉት በዚምባብዌ የተመድ የሰብዓዊ ርዳታ አስተባባሪ አላ ኑዴሁ ገልጸዋል።
« በወቅቱ የሚያስፈልገውን የሕዝቡን መሠረታዊ ፍላጎት ለማሟላት በጋራ በጀመርነው ጥረት ላይ በግብርናው፡ በአመጋገቡ ፡ በትምህርቱ እና በአኗናሩ ዘዴ ዘርፎች የተገኙት ውጤቶች ካለፉት ወራት ወዲህ እየሰራንባቸው ባሉት ዕቅዶችም ውስጥ ሊደገሙ እንደሚችል ማረጋገጥ ይሆናል። »
ከ ሚልዮኑ ዶላር ርዳታ መካከል ሰማንያ ከመቶው ባንድ ወቅት የአፍሪቃ የምግብ ቅርጫት ትባል ለነበረችው ለዚችው የደቡባዊ አፍሪቃ ሀገር ምግብ ከውጭ ለመግዣ ይውላል። ቀሪው ሀያ ከመቶ ደግሞ ኮሌራን የመሳሰሉ ተላላፊ በሽታዎችን ለመከላከያ ተግባር እና ለዉሃና ለአስቸኳይ ፍላጎቶች አቅርቦት እንደሚውል ተገልጾዋል፤ እንደሚታወሰው ከአራት ዓመታት በፊት የኮሌራ በሽታ የ 4200 ሰዎችን ሕይወት ቀጥፎዋል። በተመድ ዘገባ መሠረት፡ ከዚምባብዌ ሕዝብ መካከል ሁለት ሚልዮኑ የምግብ ርዳታ ያስፈልጋቸዋል። በወቅቱ ሀገሪቱን ለገጠማት የምግብ እጥረት ችግር የሀገሪቱ ፕሬዚደንት ሮበርት ሙጋቤ የተከተሉት የመሬት ተሀድሶ ለውጥ ፖሊሲ መሆኑን ጠበብት ይናገራሉ። በዚሁ ፖሊሲ መሠረት፡ ብዙዎን የሀገሪቱን ሰፋፊ የእርሻ ልማት ቦታ ይዘው የነበሩትን ውሁዳኑን ነጮች ገበሬዎችን በአነስተኞቹ ጥቁር የሀገሪቱ ገበሬች ተክተዋል። እነዚሁ ገበሬዎች በደቡባዊ አፍሪቃ ተደጋግሞ የሚከሰተውን ድርቅ መቋቋም ባለመቻላቸው ሀገሪቱ በምግብ እጥረት ችግር እየተሰቃየች ትገኛለች። በሰፋፊዎቹ የእርሻ ቦታዎች ከተሰማሩት ገበሬዎች እና አሁን የምግብ ርዳታ በመጠበቅ ላይ ከሚገኙት መካከል የስድሳ ዘጠኝ ዓመቱ ቲቻፋ ቺጎሞ አንዱ ናቸው። ቺጎሞ ስምንት ልጆች ያስተዳድራሉ። ከስምንቱ አምስቱ ከኤድስ ጋ በተዛመደ በሽታ ሕይወቱን ያጡት የውንድማቸው ልጆች ናቸው።
« የወንድሜን ልጆች የሚንከባከባቸው ስለሌለ የማሳድጋቸው እኔ ነኝ። ብዙ ሰብል ልሰበስብ በቻልኩ ነበር፤ ግን አካባቢያችን በከባድ ድርቅ በመመታቱ ይህ ዕቅዴ ሳይሳካ ቀረ። አሁን ምን እንደማደርግ አላውቅም። ሁኔታው እንዲህ እንዳሁኑ አሳሳቢ ሆኖ ከቀጠለ ከቀረኝ መንጋ መካከል አንዳንዱን መሸጥ እገደዳለሁ። ብዙ መንጋ ነበረኝ። ግን ድርቁ እነሱንም በመጉዳቱ ብዙዎች ሞተዋል። »
አሁን ዚምባብዌ ውስጥ የዝናብ ወራት ሲሆን፡ መኸረ ከሁለት ወራት በኋላ ሰብል ይሰበሰባል ተብሎ ይጠበቃል። ይሁንና፡ ብዙው የዚምባብዌ አካባቢ ጎርፍ እና በድርቅ እንደሚያሰጋው የአየር ፀባይ ተንባዮች ተናግረዋል። ከዚህ በተጨማሪ በወቅቱ የሚታየው የትል መንጋ በሰብሉ ላይ ያስከተለው ጉዳት ምርቱን እንደሚቀንስ ነው የሚገመተው። የዪምባብዌ የአካባቢዉ ሀገሮች ትስስርና ዓለም ዓቀፍ ትብብር ሚኒስትር ቴዲዮስ ቺፋምባ ሀገሪቱ የገጠማትን ችግር በትብብር ትወጣዋለች የሚል ተስፋ እንዳላቸው ገልፀዋል።
«በየዓመቱ ከትል መንጋዉ ጋ የተገናኘ ችግር እየገጠመን ነዉ። በመንግስትና በሰብዓዊ ተጓዳኞች መካከል በዘለቀዉ ትብብር አማካኝነት ይህ ችግር ባፋጣኝ ይወገዳል ብለን እናምናለን።»
ዚምባቡዌ አሁን ብዙውን መሠረታዊ ፍላጎትዋን ለማሟላት በዓለም አቀፍ ርዳታ ላይ ጥገኛ ሆናለች።
አርያም ተክሌ
መሥፍን መኮንን