1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

የመልካም አስተዳዳር ጥያቄ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል

ሸዋንግዛው ወጋየሁ
ማክሰኞ፣ ሐምሌ 22 2017

ለሦስት ቀናት በወልቂጤ ከተማ የተካሄደው ጉባዔ በበርካታ ጉዳዮቹ ላይ መክሯል ፡፡ የክልሉን ዓመታዊ የሥራ ሪፖርት ያደመጡት የምክር ቤቱ አባላት ትኩረት ያሻቸዋል የሏቸውን ጉዳዮች በአስተያየትም በጥያቄም መልክ አንስተዋል

አቶ እንዳሻው ጣሰው የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሠ መስተዳድር።ርዕሠ መስተዳድሩ ለክልሉ ምክር ቤት ጉባኤተኞች እንደነገሩት አገልግሎት ለመስጠት የእጅ መንሻ የሚጠይቁ አመራሮች አሉ
አቶ እንዳሻው ጣሰው የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሠ መስተዳድር።ርዕሠ መስተዳድሩ ለክልሉ ምክር ቤት ጉባኤተኞች እንደነገሩት አገልግሎት ለመስጠት የእጅ መንሻ የሚጠይቁ አመራሮች አሉምስል፦ Shewangizawe Wegayehu/DW

የመልካም አስተዳዳር ጥያቄ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል

This browser does not support the audio element.

የመልካም አስተዳዳር ጥያቄ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የህዝብተወካዮች ምክር ቤት 6ኛ ዙር 4ኛ ዓመት የስራ ዘመን መደበኛ ጉባኤውን አካሂዷል ፡፡  ለሦስት ቀናት በወልቂጤ ከተማ የተካሄደው ጉባዔ በበርካታ ጉዳዮቹ ላይ መክሯል ፡፡ የክልሉን ዓመታዊ የሥራ ሪፖርት ያደመጡት የምክር ቤቱ አባላት ትኩረት ያሻቸዋል የሏቸውን ጉዳዮች በአስተያየትም በጥያቄም መልክ አንስተዋል ፡፡ በክልሉ በታችኛው የወረዳ አስተዳደር መዋቅሮች የሚስተዋለው የመልካም አስተዳደር እጦት አሳሳቢ እየሆነ መምጣቱን  አባላቱ ተናግረዋል ፡፡

ትናንሽ መንግሥታት

በምክር ቤቱ ጉባዔ ላይ ከተነሱት ጉዳዮች መካከል በተለይ በታችኛው የአስተዳደር መዋቅሮች የሚታየው የመልካም አስተዳደር እጦት በቀዳሚነት ይጠቀሳል፡፡ አባላቱ “ ትናንሽ መንግሥታት “ ሲሉ የጠሯቸው የወረዳ አስተዳደር መዋቅሮች ለመልካም አስተዳደር እጦት ፣ ለህዝብ ብሶት እና ቅሬታ ምክንያት መሆናቸው የክልሉ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላቱ ተናግረዋል ፡፡

“ እዚህ ክልል ላይ ሲሪየስ / የምር / የሆነ የመልካም አስተዳደር ችግር እየታየ ነው “ በማለት አስተያየታቸውን የጀመሩት ሁለት የምክር ቤት አባላት “ ከላይ የክልል ካቢኔ ፣ የዞን አስተዳደር ይወስናል ፡፡ ነገር ግን ታች መሬቱ አካባቢ ሲደርስ ተፈጻሚ አይሆንም ፡፡ ምክንያቱም እዛ  “ ትናንሽ መንግሥታት “ ተፈጥረዋል ፡፡ ጉዳዮችን ለመፈጸም ፍቃደኛ አይደሉም ፡፡ እነኝህ አካላት ታች ያለውን ማህበረሰብ እያገለገሉ አይደለም ፡፡ ይህ በጣም አደገኛ ነው ፡፡ ተጠያቂነት ሊኖር ይገባል “ ብለዋል ፡፡

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 6ኛ ዙር 4ኛ ዓመት የስራ ዘመን መደበኛ ጉባኤተኖች በከፊል።ምስል፦ Shewangizawe Wegayehu/DW

ተጠያቂነት እንዴት ይሥፈን ?

ምክር ቤት አባላቱ ያነሷቸውየመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ትክክለኛ መሆናቸውን የጠቀሱት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው  ተጠያቂነትን ለማስፈን በጋራ መሥራት እንደሚገባ ጠቁመዋል ፡፡በአገልግሎት አሰጣጥ ህዝብን የሚያሰቃዩ አመራሮች መኖራቸውን የተናገሩት ርዕሰ መስተዳድሩ “ አንዳንዱ ወደ አመራርነት የሚቀላቀለው ትንሽ ጊዜ ሠርቶ የምትገኝ ነገር ካለችም ጭልፍ አርጎ ለመሄድ ነው ፡፡  በዚህ ውስጥ  ጎሰኝነቱ አለ ፡፡ የአካባቢ ሰው የሚባል ነገር አለ ፡፡ ችግሩ ውስብስብ ነው ፡፡ ነገር ግን የደረስንባቸው ላይ እርምጃ እየወሰድን እንገኛለን ፡፡ እነዚህን እያጠራን እያስተካከልን እንሄዳለን ፡፡ ለዚህ ደግሞ የሁሉንም ትብብር ሥለሚፈልግ በጋራ ልንሥራ ይገባል “  ብለዋል ፡፡

ምክር ቤቱ የተለያዩ ደንብና አዋጆችንእንዲሁም የ37 እጩ ዳኞች ሹመትን  አጽድቋል። በተጨማሪም የክልሉ የ2018  በጀት ዓመት የሚውል የ43 ቢሊየን  252ሚሊየን ብረ በጀት አጽድቋል፡፡

ሸዋንግዛው ወጋየሁ

ነጋሽ መሐመድ

ታምራት ዲንሳ

 

ቀጣዩን ክፍል እለፈው የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል እለፈው ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW