የመታመኛ ድምፅ አሰጣጥ በደቡብ አፍሪቃ
ሰኞ፣ ሰኔ 19 2009የፍርድ ቤቱ ዋና ዳኛ ሞጌንግ ሞጌንግ በትናንቱ ዕለት ባስተላለፉት ብይን መሰረት፣ ይህን ዓይነቱን የመታመኛ ድምፅ አሰጣጥ ስርዓት ማካሄድ አለማካሄድን የሚመለከተው ውሳኔ በደቡብ አፍሪቃ ምክር ቤት አፈ ጉባዔ እጅ ላይ ይገኛል።
« የብሔራዊው ሸንጎ አፈ ጉባዔ በደቡብ አፍሪቃ ሬፓብሊክ ፕሬዚደንት ላይ የሚካሄደው መታመኛ ድምፅ ስነ ስርዓት በሚስጢር እንዲሆን የመወሰን ሕገ መንግሥታዊ ስልጣን እንዳለው ተገልጿል። » ዋናው ዳኛ ግን የመታመኛ ድምፅ ስነ ስርዓት በሚስጢር ይካሄድ በሚል ትዕዛዝ ከመስጠት ተቆጥበዋል። ይህ ብይን ቀሪውን የፕሬዚደንት ዙማ የስልጣን ዘመን አዳጋች እንደሚያደርገው ይታመናል።
ከብዙ ዓመታት ወዲህ የተለያዩ የሙስና ክሶች የቀረቡባቸው እና ለሀገሪቱ ኤኮኖሚያዊ ችግሮች አስፈላጊውን ትኩረት አልሰጡም በሚል የሚወቀሱት ፕሬዚደንት ዙማ እስካሁን በምክር ቤት አራት ጊዜ የተካሄደባቸውን የመታመኛ ድምፅ ፣ በታማኝ የ«ኤኤንሲ» እንደራሴዎች ድጋፍ ተቋቁመዋል።
ዙማን የሚተቹ እና ከስልጣን እንዲነሱ የሚፈልጉ ብዙ የተቃዋሚ ፓርቲዎች የመታመኛ ድምፅ አሰጣጡ ስነ ስርዓት በሚስጢር እንዲሆን ለሕገ መንግሥታዊው ፍርድ ቤት ጥያቄ ካቀረቡ በኋላ ነበር ብይኑ የተሰጠው። እንደነዚህ ፓርቲዎች ግምት፣ በፕሬዚደንቱ ቅር የተሰኙ የገዢው አፍሪቃውያን ብሔረተኞች ኮንግረስ ፣ «ኤኤንሲ» አባላት ከፓርቲያቸው ግፊት ሳያርፍባቸው ድምፃቸውን ሊሰጡ እና የተቃዋሚዎቻቸውን ጥያቄ ሊደግፉ ይችላሉ።
የምክር ቤቱ አፈ ጉባዔ ባሌካ ምቤቴ ከብይኑ በኋላ አስተያየት ከመስጠት ተቆጥበዋል። አንድ የሀገሪቱ ራድዮ የምክር ቤቱ አፈ ጉባዔ ባሌካ ምቤቴ የመታመኛ ድምፅ ስነ ስርዓት በሚስጢር ይካሄድ በሚል ትዕዛዝ የማስተላለፍ ስልጣን እንደሌላቸው ተናግረው እንደነበር አስታውሷል። የተቃዋሚው የዴሞክራቲክ ህብረት ፓርቲ አባል ጄምስ ሴልፊ አፈ ጉባዔዋ ባሌካ ምቤቴን ቀላል ጊዜ እንደማይጠብቃቸው ገልጸዋል።
አርያም ተክሌ
ማንተጋፍቶት ስለሺ