የመጓጓዣ አገልግሎት በምዕራብ እና ቄለም ወለጋ
ረቡዕ፣ ሰኔ 25 2017
የዋጋ ጭማሪው ከተተመነው ታሪፍ ውጪ ሲሆን በተገልጋዩች ላይ ጫና ማሳደሩን ነዋሪዎች ተናግረዋል።
የቄለም ወለጋ ዞን የትራንስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሻሜ ሀቢብ የመጓጓዣ አገልግሎት ከዚህ ቀደም በግንቦት 2017 ዓ.ም ወር በተቀመጠው ታሪፍ መሠረት እየተሰጠ የሚገኝና በመንግሥት በኩል የተጨመረ ዋጋ አለመኖሩን ገልጸው ሕጋዊ ያልሆኑ የዋጋ ጭማሪዎች በአሽከርካሪዎችና ባለንብረቶች በኩል የተደረገ ሊሆን እንደሚችል ጠቁመዋል።
ከቄሌም ወለጋ ደም ዶሎ ከተማ ወደ ጊምቢ፣ ነቀምቴ እና የተለያዩ ከተማዎች በሚወሰዱ የመጓጓዣ አገልግሎት ላይ የዋጋ ጭማሪ መስተዋሉን የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች ተናግረዋል። ከደምቢ ዶሎ ወደ አቅራቢያው በሚገኙ ጫንቃ፣ መቻራ እና ሌሎች ከተሞች በመለስተኛ ተሽከርካሪዎች በሚሰጡ የመጓጓዣ አገልግሎት ላይ ከ100 ብር እስከ 150 ብር ጭማሪዎች መደረጉን ከደንቢ ዶሎ አስተያየታቸውን የሰጡን ነዋሪ አመልክተዋል።
‹‹600 ብር የነበረው ከደምቢዶሎ ነቀምቴ በሚኒባስ እስከ 1000 ብር ነው። ሀዋ ገላን ከተማ እና ጨንቃ ከተሞች በቅርበት ላይ አሉ። ወደ ሀዋ ጋላን ድሮ 30 ብር ነው አሁን ላይ 100 ብር ነው። አንድ መቶ ብር የነበረው ጫንቃ ከተማ አሁን 200 ብር ደርሷል። ምክንያት ስንጠይቅ ነዳጅ የለም ይላሉ። የመኪና እጥረትም ስላለ ሰው ባገኘው አጋጣሚ ከፍሎ ይሄዳል።››
ከምዕራብ ወለጋ ዞን ጊምቢ ከተማም ሀሳብ የሰጡን አንድ ነዋሪም ከጊምቢ ወደ ደምቢዶሎ እና ወደ ነቀምቴ መስመርም ያለው ዋጋ መጨመሩን ገልጸዋል። ከጊምቢ ወደ ደምቢ ዶሎ በፊት ከነበረው ላይ 250 ብር ያህል መጨመሩን ተናግረዋል። ናፍጣ በማደያ ላይ ባለመገኘቱ በተጠቃሚው ላይ ዋጋ እንደሚጨመሩ ነዋሪ አብራርተዋል።
‹‹ ናፍጣ ከማደያ ላይ አይገኝም። ከጊምቢ ወደ ደምቢ ዶሎ 400 ብር የነበረው አሁን 650 ነው። 60 እና 70 ብር የነበረው ናፍጣ አሁን እስለ 120 ድርስ እየተሸጠ በመሆኑ ትራንስፖርት ዋጋ ትንሽ ጨምረዋል። ያለ ታሪፍ እና ትርፍ እንዳይጫን እየተባለ አሁን አሁን ማስጠንቀቂያ ለብዙ አሽርካሪዎች ተሰጥቷል።››
‹‹በመንግሥት የተደረገ የታሪፍ ጭማሪ የለም›› የዞኑ ትራንስፖርት ቢሮ
በዚህ ጉዳይ ላይ ከምዕራብ ወለጋ ዞን አስተዳደር መረጃ ለማግኘት ያደረኩት ጥረት አልተሳካም። የቄለም ወለጋ ዞን የትራንስፖርት ቢሮ ተስተውሏል የተባለውን የዋጋ ጭማሪ በአሽከርካሪዎችና ባለንብረቶች በኩል የተደረገ እንደሆነ ገልጿል። የዞኑ የትራንስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሻሜ አብብ በዞኑ የነዳጅ እጥረት ቢኖርም ለዋጋ ጭማሪ የሚዳሪግ አለመሆኑን ገልጸው በዞኑ በኩል የተደረገ ዋጋ ጭማሪ አለመኖሩን አብራርተዋል። በተቀመጠው ታሪፍ መሰረት አገልግሎት እንዲሰጥ በሁሉም አካባቢዎች የመንገድ ተቆጣጣሪዎች እንደሚገኙ ገልጸዋል።
‹‹ የመኪና እጥት በሚገኝባቸው ቦታዎች ችግሩ ሊከሰት ይችላል። በተቀመጠው ታሪፍ መሰረት ነው አገልግሎት እየተሰጠ የሚገኘው፡፡ ነዳጅ እጥረት ይከሰታል ነገር ግን የነዳጅ እጥረት ታሪፍ የሚያስጨምር አይደለም። ከተቆጣጣሪዎች አልፎ ገንዘብ መጠየቅና ትርፍ ማስከፍል ሊኖር ይችላል። አንድ አንድ ጊዜም ነዳጅ ይጠፋል ይህንን አጋጣሚ መጠቀም ከታሪፍ ውጭ የሚያስከፍሉ እና ትርፍ የሚጭኑ አሽከርካሪዎች አሉ። ይህ ችግር ደግሞ ከተጠቃሚው ጥቆማዎች ሲቀርቡ ነው የሚቀረፈው።››
ከነቀምቴ ወደ ምዕራብ ወለጋ ዞን መንዲ እና ወደ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ አሶሳ መስመርም የመጓጓዣ አገልግሎት ላይ ከቅርብ ጊዜ ወደ ጭማሪዎች ተስተውሏል። የዋጋ ጭማሪው የሚሰተውለው ብዙ ጊዜ በመለስተኛ ሚኒባስ በሚሰጡ የመጓጓዣ አገልግሎቶች ላይ እንደሆነም ተገልጸዋል።
ነጋሳ ደሳለኝ
ሸዋዬ ለገሠ
ነጋሽ መሐመድ