«የመጽሐፍት ማዕድ» የንባብ ባህልን ማዳበር እና ትውውቅ
ዓርብ፣ መጋቢት 18 2007በጎርጎሮሲያዊ የዘመን አቆጣጠር ወር በገባ ዘወትር በመጨረሻው ዓርብ፤ ለምሳሌ በዛሬው ዕለት( 26.03.15)እና በአሁኗ ሰዓት «የመጽሐፍት ማዕድ» በመባል የሚጠራው የንባብ ዝግጅት አዲስ አበባ ውስጥ የተወሰኑ የመጽሐፍ አፍቃሪያን በተሰበሰቡበት ይቀርባል።
ሜሮን ሸዋረጋ - E-within የሚባለው ድርጅት ውስጥ የኮሚኒኬሽን ኃላፊ ሆና ታገለግላለች። የመጽሐፍት ማዕድ የንባብ ዝግጅት ከተጀመረ ሁለት ዓመት ሆነው ትላለች ሜሮን፤ ወጣቷ የዚህ ዝግጅት ዋና አስተባባሪ እና የቦርድ አባል ናት።
የ E-within ድርጅት፤ መሥራች እና ዋና ሥራ አስኪያጅ ደግሞ ሰለሞን ሲሳይ ይባላል። በግለሰብም ሆነ በድርጅት ደረጃ መጽሐፍን ሰዎች ሲያነቡ እና ሲጠቀሙ በብዛት አይስተዋልም ይላል። የመጽሐፍት ማዕድ ምሽት በሰዓት የተገደበ ነው። በተሰጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ እነ ሜሮን ብዙ ዝርዝሮች አካተዋል።
በየወሩ እየተፈራረቀ የአማርኛ እና የእንግሊዘኛ ቋንቋ መጽሐፍት ተመርጠው ይነበባሉ። የዛሬዉ የሚያተኩረዉ እንግሊዘኛ መጽሐፍ ላይ ነው። አንባቢው ደግሞ መቅደላ መኩሪያ ይባላል። መቅደላ፤ ቅዱስ ማሪያም በሚባል የግል ተቋም ውስጥ የማርኬቲንግ መምህር ነው። ከአጠናው ትምህርት ጋር የሚቀራረቡ መጽሐፎችን ማንበብ ቢያዘወትርም፤ ሎሎችንም «በመጽሐፍት ማዕድ» ፤ አንብቦ ያውቃል።
የመጽሐፍት ማዕድ ሲጀመር ከ 70 እስከ 90 ተሳታፊዎች የነበሩት ሲሆን ቁጥሩ አድጎ አሁን እስከ 200 ሰዎች እንደሚሳተፉ የፕሮግራሙ መሥራች ሰለሞን ገልፆልናል።
በመጽሐፍት ማዕድ የፌስ ቡክ ገፅ ላይ ፤ ስለ ዕለቱ የመጽሐፍ ርዕስ፤ አንባቢ እና ቦታ ከተጠቀሰ በኋላ፤ መግቢያ የሚለው ላይ፤ ጓደኛዎን ይዘው ይመጡ፤ በማለት ያስተዋውቃል። ታዳሚዎቹ ስለ ዝግጅቱ መረጃ የሚያገኙት ከዚሁ ገፅ ነው።
«የመጽሐፍት ማዕድ» በሚል ርዕስ የንባብ ባህልን ለማዳበር፣ ዕርስ በእርስ ለመተዋወቅ እና በተለያዩ ርዕሶች ላይ ለመወያየት እንዲረዳ በወር አንዴ ስለሚቀርበው ዝግጅት ነበር፤ በዛሬው የወጣቶች ዓለም ዝግጅት የዳሰስነው። ዝግጅቱን ከዚህ በታች በድምፅ ያገኙታል።
ልደት አበበ
ሸዋዬ ለገሠ