የማሊ ቀዉስና የጀርመን ጦር ዘመቻ
ሐሙስ፣ የካቲት 21 2005 የሠሜናዊ ማሊ ሙስሊም አማፂያንን የወጋዉ የፈረንሳይ ጦር የሚቆጣጠረዉን አካባቢ ለምዕራብ አፍሪቃ የልማት ማሕበረሰብ (ኤኮዋስ) ጦር አስረክቦ አካባቢዉን ይለቃል።ጀርመንን ጨምሮ የአዉሮጳ ሕብረት አባል ሐገራት በበኩላቸዉ የማሊ መንግሥት ጦርን የሚያሠለጥኑ ወታደሮችንና ባለሙያዎችን ያዘምታሉ።የኤኮዋስም ሆነ፥ የአዉሮጳ ሕብረት ጦር ተልዕኮ አሁን እንደሚታሰበዉ ባጭር ጊዜ መጠናቀቁ አጠያያቂ ነዉ።ያም ሆኖ የዶቸ ቬለዉ ዘጋቢ አሌክሳንደር ድሬክሰል እንደሚለዉ በተለይ ከአዉሮጳ ሕብረት የሚዘምቱት ወታደሮች ለረጅም ጊዜ ከማሊ ጦር ጋር ከሠሩት ከጀርመን ጓዶቻቸዉ ጠቃሚ ልምድ መቅሰም ይችላሉ።የድሬክሰለን ዘገባ ነጋሽ መሐመድ እንደሚከተለዉ አጠናቅሮታል።
ምዕራብ አፍሪቃዊቱ ሐገር የርስ በርስ ጦርነቷ ግመት፥ በመፈንቅለ መንግሥቷ ዉጥረት ከዓለም ትኩረት ከመግባቷ ከብዙ ዓመታት በፊት ጋዜጠኛ ድሬክሰለር እንደሚለዉ ከጀርመኖች ጦር አይን-ጆር እንደገባች ነበረች።እንደ ብዙዉ ዓለም ሁሉ አብዛኛዉ ጀርመናዊዉም ወታደሮቹ ማሊ መዝመታቸዉንም ሆነ፥ የሚያደርጉትን አያዉቅም።
የጀርመን ወታደሮችን ግን እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር ከሁለት ሺሕ አምስት ጀምሮ የማሊን ጦር ሲያሰለጥኑ፥ ሲያደራጁና ሲረዱ ነበር።«የማሊ ጦርን ሥንረዳ፥ ጥንስስ የሚሆኑ ሐይላትን ሥናሰለጥን ነበር።ይሕ ሐይል ለኤኮዋስ ሠራዊት እንደ እርሾ ሊያገልግል ይችላል።የግንባታና የመካኒኮች ማሠልጠኛ ማዕከል መሥርተናል።»ይላሉ ሥም ማዕረጋቸዉን መግለፅ ያልፈለጉት በማሊ የጀርመን የአማካሪዎች ጓድ አዛዥ።
በረሐማይቱ፥ ጥንታዊቱ፥ ደሐይቱ ሐገር በርስ በርስ ጦርነት ሥትተረማስ፥ በመፈንቅለ መንግሥት ስትታበጥ ባለፈዉ አመት ሚያዚያ የአማካሪዎቹ ጓድ ወደ ሐገሩ ተመለሰ።የጓዱ አዛዥ ዘንድሮ የካቲት ተመስልሰዉ ወደ ባማኮ ሔደዋል።ያሁኑ ተልዕኮ ዓለም ያወቀዉ፥ ብዙዉ አዉሮጳ የሚያተፍበት፥ ከበፊቱ የተለየ።
የበፊቱ ተዕልኮ ከተጀመረበት ከሁለት ሺሕ አምስት ጀምሮ አምና እስከተቋረጠበት ጊዜ ድረስ ጀርመን ለማሊ ጦር ከከባድ ካሚዮኖች እስከ የግንባታ ማሺኖች፥ ከጀልባ እስከ ድንኳን፥ ሁሉ በሁሉ ሰላሳ-ሰባት ሚሊዮን ዩሮ የሚያወጣ ቁሳቁስ ለማሊ ጦር ረድታለች።አሁንም የአዉሮጳ ሕብረት በወሰነዉ መሠረት የጀርመን ፌደራላዊ መንግሥት አርባ አሰልጣኝ ወታደሮችን ወደ ማሊ ለማዝመት አቅዷል።
የተጣማሪዉ መንግሥት አባል የነፃ ዲሞክራቶቹ ፓርቲ (FDP) የምክር ቤት እንደራሴና የመከላከያ ጉዳይ አዋቂ ኤልከ ሆፍ እንደሚሉት መንግሥታቸዉ በጀመረዉ መቀጠሉ ተገቢ ነዉ።
«ፈርቀዳጆቹን አሰልጥነናል።እንቀጥላለንም።ምክንያቱም ሠልጣኞቹ ማሊን በመሠለች ሐገር የሚያከናዉኑት ምግባር በጣም አስፈላጊ ነዉ።ሥልጠናዉ ፈንጂዎችን ማክሸፍን፥ መንገድና ድልድዮችን መገንባትን የሚያካት በመሆኑም ጠቃሚ ነዉ።»
የቀድሞዉ የአሠልጣኞች ቡድን አዛዥም በዚሕ ይስማማሉ።የማሊ ጦር ባልደረቦችም የሥልጠናና የቁሳቁስ ርዳታ ከተደረገላቸዉ አዛዡ እንደያምኑት ሐላፊነታቸዉን ለመወጣት ብቁ ናቸዉ።የአዉሮጳ ሕብረት በወሰነዉ መሠረት የማሊን ጦር ለማሰልጠን የሚዘምቱት ወታደሮች እዚያ የሚቆዩት ለዘጠኝ ወራት ያሕል ነዉ።ጊዜዉ የመጀመሪያዉን ዙር ሥልጠና ለመስጠት አያንስም። የጀርመኑ የጦር መኮንን እንደሚሉት ግን ለማሊ ጦር ተገቢዉን ሥልጠና ለመስጠት ረዘም ያለ ጊዜ ማስፈለጉ አይቀርም።
«ከረጅም ጊዜ አኳያ፥ እኔ እንደሚመስለኝ፥ ሥልጠናዉን ለማጠናከርና ፕሮጀክቱ ሙሉ በሙሉ ገቢናዊ መሆኑን ለመከታተል አራት ተጨማሪ ዓመታት ያስፈልጋሉ።»
በቅርቡ ማሊን፥ ኒዠርና አልጄሪያን የጎበኙት የወታደራዊ ጉዳይ አዋቂዋ ኤልከ ሆፍ የማሊ ጦር ተከታታይ ሥልጠና እና ድጋፍ እንደሚያስፈልገዉ ያምናሉ።ወታደራዊዉ ዉጊያ፥ ሥልጠናዉም ሆነ ድጋፉ ግን ሆፍ እንደሚያምኑት ጊዚያዊዉን ችግር ከማቃለል ባለፍ ፖለቲካዊዉን መፍትሔ ሊተካ አይችልም።
ነጋሽ መሐመድ
አርያም ተክሌ