የማሊ ጦርነት፥ ጅምላ ግድያና ሊቢያ
ሐሙስ፣ ጥር 16 2005 24 01 13
ከፈረንሳይና ከማሊ መንግሥት ጦር አብረዉ ሠሜናዊ ማሊን የሚቆጣጠሩትን ሙስሊም አማፂያንን እንዲወጉ የአፍሪቃ ሐገራት ያዘመቷቸዉ ወታደሮች ማዕከላዊ ማሊ ዉስጥ እየሰፈሩ ነዉ።የሠብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች በበኩላቸዉ የማሊ መንግሥት ጦር በአማፂነት የጠረጠራቸዉን ሰዎች በጅምላ ገድሏል በማለት ድርጊቱን ተቃዉመዋል።ሠማናዊ ማሊን ከሚቆጣጠሩት አማፂያን አንዱ ለሁለት መከፈሉ ዛሬ ሲነገር፥ አንዳድ ተዋጊዎች ሠሜናዊ ማሊን እየለቀቁ አልጄሪያ፥ ኒዠርና ሊቢያ መግባታቸዉ ተዝግቧል።የማሊዉ ጦርነት ሊቢያን ያመሠቃቀለዉ ጦርነት ዉጤት መሆኑን የፖለቲካ ተንታኞ እየተቹበት ነዉ።ነጋሽ መሐመድ አጭር ዘገባ አለዉ።
የፈረንሳይ ጦር እና የማሊ መንግሥት ተባባሪዉ በያዝነዉ ሳምንት መጀመሪያ ዲያባልይ እና ዶኡንቴዝ የተባሉትን ሁለት ከተሞች ከመቆጣጠራቸዉ ባለፍ አዲስ ያስመዘገቡት ድል የለም።ፓሪሶች ግን አስደሳች ዜና አላጡም።ካንድም፥ ሁለት።
ከፈረንሳይ ወታደሮች ጋር አብረዉ አማፂያኑን እንዲወጉ የምዕራብ አፍሪቃ የምጣኔ ሐብት ማሕበረሰብ (ኢኮዋስ) አባል ሐገራት ያዘመቷቸዉ ወታደሮች ከርዕሠ-ከተማ ባማኮ ተነስተዉ ማዕካላዊ ማሊ እሠፈሩ ነዉ።የኤኮዋስ አባል ሐገራት ሊያዘምቱት ካዘጋጁት ሰወስት-ሺሕ ሰወስት መቶ ጦር-አንድ ሺሕዉ ማሊ ገብቷል።
ከአንድ ሺዉ ጦር ገሚሱ ዛሬ ማዕከላዊ ማሊ መስፈር ጀምሯል።የፈረንሳዩ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ሎራ ፋቢዩስ የአፍሪቃ ጦር በዚሕ ፍጥነት ማሊ ይደርሳል ብለዉ አልገመቱም ነበር።እና ፍጥነቱን ሚንስትሩ «አስደናቂ» አሉት።ቻድ የኢኮዋስ አባል ባትሆንም ፕሬዝዳት ኢድሪስ ዴቢ የሐገራቸዉ የቀድሞ ቅኝ ገዢ ፈረንሳይ ከምትመራዉና ከምታስተባብረዉ ዘመቻ አልቀርም ብለዉ፥ ሁለት ሺሕ ወታደር ሊያዘምቱ ተዘጋጅተዋል።ይሕም ለፓሪሶች አስደሳች ነዉ።
የማሊ መንግሥት ጦር በአማፂነት የጠረጠራቸዉን ሰዎች በጅምላ የመግደሉ ግፍ ከሰብአዊ መብት ተሟጋቾች ጆሮ መድረሱ ግን ለፓሪሶች መጥፎ፥ ለባማኮ ጦር አዛዦች ደግሞ አሳሳቢ ዜና ነዉ።ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ፌደሬሽን የተሰኘዉ የመብት ተሟጋች ድርጅት እንዳስታወቀዉ የማሊ ወታደሮች መልካቸዉ ፈካ፥ ፈካ ያለ ሰዎችን እየለቀመ በጅምላ ገድሏል።መንበሩን-ፓሪስ ፈረንሳይ ያደረገዉ የመብት ተሟጋች ድርጅት እንዳስታወቀዉ የማሊ ወታደሮች ሴቫሬ በተባለችዉ ከተማና አካባቢዋ ከሠላሳ በላይ ሰዎችን ሳይገድል አልቀረም።ባካባቢዉ የሠፈረዉ ጦር አዛዥ ሌትናንት ኮሎኔል ዲራ ኮኔ ጉዳዩን እናጣራለን ብለዋል።
«እኛ እንደ ጦር ሠራዊት እዉነታዉ እንዲወጣ በሙሉ አቅማችን እንጥራለን።ባሁኑ ሰዓት ዓለም ዓቀፉ ማሕበረሰብ ለኛ ድጋፍ የሚሰጠዉና የሚረዳንም ይሕንን ሥናደርግ ነዉ»
በዉጊያ፥ ዘመቻዉ፥ በግድያ ወቀሳዉ መሐል ሰሜን ማሊ ዉስጥ ከሸመቁት ትላልቅ አማፂ ቡድናት መሐል አንዱ አንሳር ዲን ለሁለት መሠንጠቁ ተዘግቧል።ከዋናዉ ቡድን አፈንግጠዉ የዛዋድ ንቅናቄ የሚል አንጃ መመሥረታቸዉን ያስታወቁት ሸማቂዎች ለመደራደርም ጠይቀዋል።የቱአሬግ ጎሳ ታጣቂዎች የሚበዙበት አንሳር ዲን የፈረንሳይ ጦር ጥቃት ከመክፈቱ በፊትም ከማሊ ጊዚያዊ መንግሥት ጋር ድርድር ጀምሮ ነበር።
ሌሎች አማፂያን ደግሞ ሰሜናዊ ማሊን እየለቀቁ ወደ አልጄሪያ፥ ኒጀርና ወደ ሊቢያ መሠደዳቸዉ ተዘግቧል።በቡድንና በግል በተለይ ወደ ሊቢያ የሚሸሹት ታጣቂዎች የኮሎኔል ሙዓመር ቃዛፊ አገዛዝ ሲወገድ ከሊቢያ ወደ ማሊ የተሻገሩ ሳይሆኑ አልቀሩም።የደቡብ ሊቢያ ነዋሪዉ አብድል ባሲጥ እንደሚለዉ ታጣቂዎቹ ወደ ሊቢያ መግባታቸዉ ለሊቢያ አስጊ ነዉ።
«የሊቢያ ጠረፋማ አካባቢ ፀጥታ በጣም ያሳስበናል።እነዚሕ ሚሊሺያዎች ማሊ ያደረጉትን ሊቢያ ዉስጥ ሊፈፅሙት ይችላሉ።የማሊን ሕዝብ ብቻ ሳይሆን ሁሉንም የሚያሰጉ ናቸዉ።»
ለቱአሬግ ጎሳ አባላት መብትና ነፃነት ከሚፋለሙት ታጣቂዎች ብዙዎቹ በኮሎኔል ሙዓመር ቃዛፊ አገዛዝ ዘመን የቢሊያ ጦር ባልደረባ የነበሩ ናቸዉ።የቃዛፊ መንግሥት በምዕራባዉያን ሐገራት ጦር ድብደባና በአማፂያን ዉጊያ ሲወገድ የቱአሬግ ወታደሮች ከነ-ትጥቃቸዉ ወደ ማሊ ተሻግረዋል።
ነጋሽ መሐመድ
ሸዋዬ ለገሠ