1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ
ኅብረተ ሰብሰሜን አሜሪካ

የማኀበረ ግዩራን የሽልማት ሥነ ስርዓት

ታሪኩ ኃይሉ
ሐሙስ፣ ግንቦት 21 2017

ለሃገራቸውንና ለማኀበረሰባቸው የላቀ አስተዋጽኦ ያበረከቱ ግለሰቦችና አንድ ድርጅት በዩናይትድስቴትስ ከሚገኘው "ማኀበረ ግዩራን ዘረ ኢትዮጵያ" የክብር ተሽላሚ ሆኑ። ግብረ ሰናይ ድርጅቱ ሜሪላንድ ውስጥ ባካሄደው ሥነ ስርዓት በትምህርታቸው ከፍተኛ ውጤት ላስመዘገቡ ተማሪዎችም የማበረታቻ ሽልማት መስጠቱን የድርጅቱ ኃላፊዎች ለዶቼ ቬለ አስታውቀዋል።

USA Atlanta 2025 | SEED-Jubiläum | Studenten-Ehrung mit Künstler Rophnan
ምስል፦ SEED

የማኀበረ ግዩራን የሽልማት ሥነ ስርዓት

This browser does not support the audio element.

ማኀበረ ግዩራን ዘረ ኢትዮጵያ ወይንም በእንግሊዝኛ ምህፃሩ ሲድ፣በኢትዮጵያና በዚህ በዩናይትድ ስቴትስ በተለያዩ የሙያ ዘርፎች ከፍተኛ አስተዋጾኦ ላደረጉ ድርጅቶችና ግለሰቦች የዕውቅና ሽልማት በመስጠት፣ ዘንድሮ 32 ዓመት ሆነው። ድርጅቱ በዚህ መስክ፣አሜሪካ ውስጥ ለረጅም ጊዜ ካገለግሉ የትውልደ ኢትዮጵያውያን ድርጅቶች መኻከል አንዱ መሆኑን፣ መስራችና ፕሬዚደንቱ አቶ አክሊሉ ደምሴ ለዶቼ ቬለ ገልጸዋል።

የማኀበረ ግዩራን ዘረ ኢትዮጵያ ዕውቅናና ሽልማት

"የዘንድሮ፣32 ዓመታችን ነው፤ለብዙ ጊዜ ኖረናል። የዘንድሮው ከሌሎች ጊዜያት ለየት የሚያደርገው አንደኛውና ዋነኛው  የምንለው፣በምስራቃዊ ዳርቻ ያሉ ሰዎች ነበሩ ተማሪዎች የሚጠቁሙት፤ ዘንድሮ ግን ከሲያትል ዋሽንግተን፣ከኦሃዮ፣ከሂውስተን ቴክሳስ እና እነዚህን ከመሳሰሉ ቦታዎች እና ከቨርጂኒያ ፣ከፊላዴልፊያ፣ከዋሽንግተን ነው ተማሪዎቹ የመጡት። እና ይሄ የሚያሳየው አሜሪካ ውስጥ የተስፋፋ ዕውቀት አለው ማለት ነው ማኀበረ ግዩራን ዘረ ኢትዮጵያ።"

ተሸላሚዎቹ  እነማን ናቸው?

ሲድ ኢትዮጵያ፣ዘንድሮ ዕውቅና ስለሰጣቸው ግለሰቦችና አንድ ድርጅት አበርክቶን በተመለከተ፣ የማኀበረ ግዩራን ዘረ ኢትዮጵያ ምክትል ፕሬዚዳንት ዶክተር ሰለሞን ገብሩ እንደሚከተለው አስረድተዋል።

የማኀበረ ግዩራን ዘረ ኢትዮጵያ ምክትል ፕሬዚዳንት ዶክተር ሰለሞን ገብሩምስል፦ SEED

"በተለይም ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ኃይማኖት ጋር በተያያዘ የቅርስ ጥበቃ የሚያደርገው ሐመረ ብርሃን፣ አቶ አጎናፍር ሽፈራው፣ ዶክተር ሞገስ ገብረማርያም፣ በህክምና ውስጥ በዚህ በከተማውና አከባቢው ብዙ ዓመት ያገለግሉ ለሕብረተሰባችን፣እንደዚሁም ደግሞ አርቲስት ሮፍናን እና ዶክተር ተሰማ ገብረ እግዚአብሔር ናሽናል ሳይንስ ፋውንዴሽን ውስጥ ትልቅ ሳይንቲስት የሆነ እና አርቲስት ተስፋዬ ሲማን፣ ድርጅታችን ተሸላሚ አድርጓል።"

የካንሰር ተመራማሪው የ“ሲድ” ሽልማት አገኙ

ይኸው አንጋፋ ድርጅት፣መልካም ለሰሩ ኢትዮጵያውያን ግለሰቦችና ድርጅቶች ሽልማትና አክብሮት ከመቸር በተጨማሪ፣በትምህርታቸው የላቀ ውጤት ያስመዘገቡ ተማሪዎችንም መርጦ በመሸለም ማበረታቱን ዶክተር ሰሎሞን ገልጸዋል።

"አዳጊ የሆኑ፣ወደፊት ደግሞ ኮሌጅ በመግባት ለኢትዮጵያ ትልቅ አስተዋጽኦ ሊያበረክቱ ይችላሉ የሚላቸውን የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች የተለያየ መመዘኛዎች በማውጣት፣ከፍተኛ ጂፒኤ ያመጡ፣የኮሌጅ ትምህርታቸውንም በብዛት የወሰዱ ልጆችን  ከስድስት ሰባት ግዛቶች፣ከፔንሲልቫኒያ፣ከኦሃዮ፣ከፊላዴልፊያ፣ከቨርጂኒያ፣ከዋሽንግተን ዲሲ እንደዚሁም ቴክሳስ ስምንት ልጆችን ሸልሟል።እነዚህ ስምንት ልጆች በተለያየ ጥሩ ጥሩ ትምህርት ቤቶች ውስጥ ተቀባይነት አግኝተው ወደ ዩኒቨርሲቲ ለመግባት  እየተዘጋጁ ነው።"

ድርጅቱ ያበረከተው ፋይዳ

ማኀበረ ግዩራን ዘረ ኢትዮጵያ፣ ምሳሌነት ያላቸውን ሰዎች በማበረታታት፣ተተኪው ትውልድ በሥነ ምግባርና በሙያ እንደታነጹ በማድረግ፣ትልቅ  የሆነ ፋይዳ እያበረከተ መሆኑን ከፕሬዚዳንቱ ገለጻ ለመረደት ተችሏል።

"በሕይወት እያሉ ሰዎችን ማክበርና ለልጆቻችን ትልልቅ ምሳሌ ይሆናሉ ተብሎ፣ ከራሳችን ወገኖች ለልጆቹ ስናሳያቸው፣እነዛ ልጆች  የሚጠበቅባቸውን አደራ ከትልልቆቹ እያዩ፣ ደግሞ ተመልካች ውስጥ ያሉት ህፃናት ልጆች የከፍተኛ ተመራቂዎችን እያዩ በጣም እየተነሳሱ ብዙ ቦታ ደርሰዋልና እዚህም ሃገር አሁንም ቢሆን ባሉበት በህክምናም  ሆነ በሙዚቃ በማንኛውም መስክ ያሉ ሰዎች ትልቅ ቦታ የደረሱ ወገኖቻቸውንና ሃገራቸውን እንደሚረዱ አንጠራጠርም።"ብለዋል።


ታሪኩ ኃይሉ
እሸቴ በቀለ
ታምራት ዲንሳ 
 

ቀጣዩን ክፍል እለፈው የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል እለፈው ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW