የማዕከላዊ አፍሪቃና ዩኒሴፍ
ሐሙስ፣ ጥር 2 2005 በማዕከላዊው አፍሪቃ ሪፐብሊክ ለውትድርና የሚመለመሉ ህጻናት ቁጥር መጨመር እንዳሳሰበው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የህጻናት መርጃ ዩኒሴፍ አስታወቀ። አማጺ ቡድኖችና መንግስትን የሚደግፉ ሚሊሻዎች ልጆች በወታደራዊ ግጭቶች ውስጥ እንዲሳተፉ እያስገደዱ መሆኑን ድርጅቱ ገልጿል። በማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብክ የዩኒሴፍ የአደጋ ጊዜ እርዳታ አስተባባሪ ሚስስ ሻኖን ሽትሮተር ጋር ኢሳቅ ሙጋቢያ ደረገውን ቃለምልልስ ገመቹ አሰናድቷል።
ከማዕከላዊው አፍሪቃ ሪፐብሊክ መንግስት ጋር የተደረሰው ስምምነት ተፈጻሚነት አላገኘም በሚል ምክንያት ስሌካ የሚባል የአማጺያን ቡድን ባለፈው ታህሳስ ወር መንግስት ላይ ካመጸ ወዲህ፤ በሀገሪቷ አለመረጋጋት ሰፍኗል። በዚም ምክንያት አማጺያኑና የመንግስት ሚሊሻዎች ለአቅመ አዳምና ሄዋን ያልደረሱ ህጻናትን ለውትድርና እየመለመሉ ነው ይላሉ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የህጻናት መርጃ፣ የማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ ተጠሪ ሚስስ ሻሮን ሽትሮተር፤
«ትክክለኛ የሆነ ቁጥር ባይኖረንም፣ ከተለያዩ ዓለም አቀፍና ሀገር አቀፍ አጋሮቻችን ባገኘነው መረጃ መሠረት፣ ታጣቂ ቡድኖች፣ አማጺያኑና የመንግስት ደጋፊ ሚኒሻዎች ህጻናትን ለውትድርና እየመለመሉ ነው። በተጨማሪም ከዚህ በፊት ከኚህ ነፍጥ ያነገቡ ቡድኖች ጋር ትስስር የነባራቸው ልጆችም መልሰው ተመልምለዋል።»
እነኚህ አማጺያንና ሚሊሻዎች ህጻናቱን ጠብመንጃ እንዲይዙ ብቻ አይደለም የሚያስገድዷቸው። ሲሹ ስንቅና ትጥቃቸውን ያሸክሟቸዋል። ከዚህም አልፎ የወሲብ መጠቀሚያ ያደርጓቸዋል። በቅርቡ በማዕከላዊ አፍሪቃ የተከሰተው ቀውስ ከመታየቱ በፊት 2500 የሚደርሱ ህጻናት የታጣቂ ቡድኖቹ ታዋጊዎች ሆነው አገልግለዋል። ዩኒሰፍም እኚህ ህጻናት ወደ ማህብረሰባቸው ተመልሰው ሰላማዊ ኑሮ መምራት እንዲችሉ ሲሰራ ቆይቷል፥
«ለውትድርና የተመለመሉ ህጻናትን እና ከታጣቂ ቡድኖች ጋር በታዋጊነት ወይም በወሲብ ባሪያነት የተሳሰሩ እኚህን ህጻናት ከውትድርና ማሰናበትን በተመለከተ፣ ከማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ ጋርና CPJP እንዲሁም UFDR ከተሰኙ ታጣቂ ቡድኖች ጋር በቅርበት እየሰራን ነው።» ለዓመታት ከነሱ ጋር ስንሰራ ቆይተናል። አሁንም ከዩኒሴፍ ጋር የልጆችን መብት ለመከላከል እንዲሰሩና ልጆችን ለውትድርና መመልመል እንዲያቆሙ፣ እንዲሁም የተመለመሉትን ደግሞ እንዲመልሷቸው ማበረታታችንን እንቀጥልበታለን።»
በቅርቡ በማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ የተቀሰቀሰው ቀውስ ይህን ጥረት ይጎዳል የሚል ስጋት አላቸው፤ ሚስስ ሽትሮተር፣ በፖሊቲካዊው ቀውሱ ምክንያት ከቤተሰቦቻቸው የተለዩ ልጆች በተለይ ለአደጋው እየተጋለጡ መሆናቸው ተነግሯል፣
«አሁን እንደ አዲስ ከተጀመረው ግጭት ጋር ተያይዞ ልጆቹ ከማህረሰቦቻቸው ጋር መልሰው እንዲላመዱ የማድረጉ ጥረት ምን ሊሆን እንደምችል እያሳሰበን ነው። ቀድሞውኑ እነኚህን ልጆች ከቤተሰቦቻቸው ጋር ብቻ ሳይሆን ከአካባቢያቸው ህብረተሰብ ጋር ማዋሓዱ አስቸጋሪ ነበር። ምክንያቱም ለውትድርና ከተመለመሉ በኃላ ያሳለፉት ህይወት ከአንዱ ወደ ሌላኛው የተለያየ ነውና።»
አብዛኛዎቹ የማዕከላዊ አፍሪቃ ዜጎች በስጋትና ፍርሃት ውስጥ በሚገኙበት በአሁኑ ወቅት በርግጥ እነኚህን ልጆች ከሌሎች ልጆች ጋር በአንድ ዓይን አያዩዋቸውም። ለልጆቹም መልሰው የማህበረሰባቸው አካል መሆን አዳጋች ይሆንባቸዋል። ዩኒሰፍና ሌሎች አጋሮቹ እኚህ ልጆቹ በማህበረሰባቸው መልሰው እንደ ልጆች መታየት እንዲችሉ ከማህበረብ መሪዎች ጋር እየሰራ መሆኑን ሻኖን ሽትሮቴር ገልጸዋል።
እአአ በ1989 የጸደቀው የተባበሩት መንግስታት የህጻናት መብት ድንጋጌ ከ15 እድሜ በታይ ያሉ ህጻናት በምንም መልኩ ለውትድርና መመልመልና በዬትኛው የነፍጥ ግጭት ውስጥ መሳተፍ እንደሌለባቸው ይደነግጋል።
ገመቹ በቀለ
አርያም ተክሌ