የምግብ እርዳታ የጫኑ መኪናዎች ከግብፅ ወደ ጋዛ ዛሬ ገቡ
እሑድ፣ ሐምሌ 20 2017
በጋዛ እየተባባሰ ያለውን ሰብአዊ ቀውስ ለማቃለል የመጀመሪያወቹ የእርዳታ መኪኖች ፍልስጤም ግዛት መድረሳቸው ተገለፀ። እስራኤል የምግብ አቅርቦትን ለማገዝ በአንዳንድ አካባቢዎች ጦርነቱን እንደምታቆም አስታውቃለች።
የእርዳታ መኪናዎች ከግብፅ ወደ ጋዛ መግባት መጀመራቸውን የግብፅ የመንግስት መገናኛ ብዙሃን ዛሬ ማለዳ ዘግበዋል።ርምጃው እስራኤል በፍልስጤም ግዛት ያለውን ሰብአዊ ቀውስ ለማቃለል ከፍተኛ ጥረት እንደምታደርግ ካስታወቀች ከሰዓታት በኋላ ነው።"የግብፅ የእርዳታ መኪኖች በራፋህ መሻገሪያ በኩል ወደ ጋዛ ሰርጥ መግባት ጀመሩ" ሲል አልቃሄራ ኒውስ የተባለው የዜና ምንጭ በ X ገፁ ላይ አስፍሯል ።ከስዓታት በኋላም በጋዛ እየተባባሰ ያለውን ሰብአዊ ቀውስ ለማቃለል የመጀመሪያወቹ የእርዳታ መኪኖች ፍልስጤም ግዛት መድረሳቸው ተሰምቷል።
እስራኤል በጦርነት ለተጎዳው የፍልስጤም ግዛት የእርዳታ አቅርቦትን እየገደበች ነው በሚል ለወራት ውንጀላ ሲቀርብባት ቆይቷል።ይህንን ግፊት ተከትሎ እስራኤል በአውሮፕላን የምግብ እርዳታ መጣል መጀመሯን ትናንት አስታውቃ ነበር።የእስራኤል ጦር በበኩሉ የተባበሩት መንግስታት የእርዳታ መኪኖችን ለጋዛ ነዋሪዎች ምግብ እና ሌሎች አስፈላጊ ቁሳቁሶችን እንዲያደርሱ "የሰብአዊ ኮሪደሮች” መከፈታቸውንም ገልጿል።ጦሩ ብዙ ህዝብ በሚበዛባቸው አካባቢዎች የሚደረገውን ውጊያ «የሰብአዊ እርዳታ ፋታ» በሚል የእርዳታ ድርጅቶችን ምግብ እና ሌሎች ቁሳቁሶችን ለማድረስ በሦስት የጋዛ አካባቢዎች የሚካሄደውን ውጊያ እንደሚያቆም ዛሬ አስታውቋል።የተኩስ አቁሙ የሚተገበረው በአል-ማዋሲ፣ በዲር አል-ባላህ እና በጋዛ ከተማ ሲሆን፤ በየቀኑ ከጠዋቱ 4 ስዓት እስከ ቀኑ 11 ስዓት የሚቆይ ነው።
የእስራኤል ጦር” ስልታዊ ፋታ” ሲል የጠራው ይህ የተኩስ ማቆም ውሳኔ ፤ እስራኤል በፍልስጤም ግዛት ውስጥ ያለውን ሰብዓዊ ቀውስእንድታቃልል ከፍተኛ ዓለም አቀፍ ግፊትን ተከትሎ የመጣ ነው።ምንም እንኳን እስራኤል የምግብ አቅርቦትን እየገደበች ነው የሚለውን ባትቀበለውም፤የረድኤት ድርጅቶች ባለፈው ሳምንት በጋዛ ህዝብ ላይ ከፍተኛ ረሃብ መኖሩን አስጠንቅቀዋል።
በሃማስ የሚተዳደረው የጋዛ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር እንዳለው ባለፉት ጥቂት ሳምንታት ውስጥ በርካታ ፍልስጤማውያን በምግብ እጦት ሞተዋል።
እስራኤል በግንቦት ወር አዲስ እገዳዎችን እንደገና ከመጣሏ በፊት በመጋቢት ወር በጋዛ ሁሉንም አቅርቦቶች አቋርጣለች።እስራኤል በእርዳታ አቅርቦት ላይ ባደረገችው ገደብ በጋዛ ረሃብ እንደሚከሰት ባለሙያዎች ሲያስጠነቅቁ ቆይተዋል።ባለፉት ሳምንታት የምግብ ማከፋፈያ ቦታዎች ላይ ለመድረስ ሲሞክሩ በመቶዎች የሚቆጠሩ ፍልስጤማውያን ተገድለዋል።
ፀሀይ ጫኔ
ዮሀንስ ገብረእግዚአብሄር