1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሞሮኮና የፖሊሳርዮ ነፃ አውጭ ንቅናቄ ድርድር

ሰኞ፣ ሰኔ 11 1999

የምዕራብ ሰሀራ ጉዳይ ከዓለማችን የተረሱ ግጭቶች አንዱ እስከመሆን ደርሷል

የሞሮኮ መንግስትና የፖሊሳርዮ ነፃነት ንቅናቄ ዛሬ ኒውዮርክ ውስጥ ቀጥተኛ ንግግር ያደርጋሉ ። ይኽው በተባበሩት መንግስታት ድርጅት አማካይነት የሚካሄደው ድርድር በመንግስትና በንቅናቄው መካከል ለለሰላ ሁለት ዓመታት የዘለቀውን ግጭት ያስወግዳል የሚል ተስፋ ተጥሎበታል ። ለሁለት ቀናት የሚካሄደውን ንግግር የሚመሩት የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሀፊ ባንኪሙን የምዕራብ ሰሀራ መልዕክተኛ ፒተር ቫን ቫልሰም ናቸው ። በዚሁ ስብሰባ ላይ የአልጀሪያ እና የሞሪታኒያ ተወካዮችም ይገኛሉ ። እአአ በሺህ ዘጠኝ መቶ ሰባት አምስት ነበር ሞሮኮ ምዕራብ ሰሀራን በኃይል ወደ ራስዋ ያቀላቀለችው ። በአልጀሪያ የሚደገፈው የፖሊሳርይዮ ነፃ አውጭ ንቅናቄም ይህን በመቃወም ግዛቲቱ ነፃ እንድትወጣ ሲታገል ቋይቷል ። በአሁኑ ሰዓት ግን የምዕራብ ሰሀራ ጉዳይ ከዓለማችን የተረሱ ግጭቶች አንዱ እስከመሆን ደርሷል ። እንደሌሎቹ ግጭቶች ችግሩ ጎልቶ ስለማይሰማ በብዙዎች ዘንድ ያለው አስተሳሰብ ሁኔታው ባለበት መልኩ ይቀጥላል የሚል ነው ። በፍሬድሪክ ኤበርት ድርጅት የሰሜን አፍሪቃ ተንታኝ ሀዮ ላንዝ
“የዓለማችን ማህበረሰብ ከዚህ ዓይነቱ ሁኔታ ጋር ነው የሚኖረው ። ከአሁን በኃላ ምንም ጦርነት አይኖርም ከሚለው ጋር ። በአሁኑ ሰዓት የተኩስ አቁም አለ ፤ በዚህ ሁኔታም ህዝቡ መኖር ይችላል “
ተንታኙ ላንዝ ይህን ቢሉም የምዕራብ ሰሀራ ጉዳይ ሲጤን ችግሩ ደም አፋሳሽ አልነበረም ማለት አይቻልም ። ሞሮኮ እአአ በሺህ ዘጠኝ መቶ ሀምሳ ስድስት ነፃ ከወጣች አንስቶ በፎስፌት ማዕድን የበለፀገችው ምዕራብ ሰሀራ ትሰጠኝ ስትል ጥያቄዋን ከማንሳት ወደ ኃላ አላለችም ነበር ። ሞሮኮ ነፃ ከወጣች በኃላም ምዕራብ ሰሀራ የስፓኝ ቅኝ ነበረች ። እአአ በሺህ ዘጠኝ መቶ ሰባ ሶስትም የተወሰኑ ወጣቶች ታዋቂውን የፖሊሳርዮ ንቅናቄ መሰረቱ ። የንቅናቄው ዓላማም ምዕራብ ሰሀራን ነፃ ማውጣት ነበር ። ከአንድ ዓመት በኃላ ደግሞ ሞሮኮ ዘሄግ ለሚገኘው ለዓለም ዓቀፉ ፍርድ ቤት የምዕራብ ሰሀራን የይገባኛል ጥያቄ አቀረበች ። ፍርድ ቤቱም አንዳንድ የምዕራብ ሰሀራ ጎሳዎች ከሞሮኮው ንጉስ ጋር የተያያዘ የዘር ሀረግ እንዳላቸው ከማረጋገጥ በስተቀር ግዛቲቱ ለሞሮኮ ትሰጥ የሚል ውሳኔ ሳያሳልፍ ቀረ ። የምዕራብ ሰሀራ ጉዳይ በዚህ ሁኔታ ላይ እያለ እአአ በሺህ ዘጠኝ መቶ ሰባት አምስት በግዛቲቱ ታሪክ ውስጥ ትልቅ ለውጥ የሚያስከትል ሁኔታ ተፈጠረ ። የስፓኙ አምባገነን መሪ ጀነራል ፍራንኮ በሞቱበት በዚህ ወቅት ላይ የሞሮኮው ዳግማዊ ንጉስ ሀሰን ሰላማዊ ሰዎች ናቸው የታባሉ ቁጥራቸው ወደ ሶስት መቶ ሀምሳ ሺህ የሚጠጋ ሰዎች አደራጅተው ወደ ግዛቲቱ ላኩ ። በዚህ ጊዜም ምዕራብ ሰሀራ የነበረው የስፓኝ ጦር አንዳችም የመከላከል ሙከራ ሳያደርግ ሰዎቹን አስገብቶ ግዛቲቱን ለቆ ወጣ ። ይህም ለምዕራብ ሰሀራ ግጭት መነሻ ሆነ ። ሞሮካውያኑ ወደ ምዕራብ ሰሀራ ሲገቡ አስር ሺህ የሚሆኑ ሳሀራውያንን ከግዛቲቱ ወጥተው ወደ አልጀሪያዋ ቲንዱፍ ከተማ ተሰደዱ ። ከዚያን ጊዜ አንስቶም የፖሊሳርዮ ግንባር በደፈጣ ውጊያ ተሰማራ ። በመንግስትና በተቃዋሚዎች መካከል በተካሄደው ውጊያም በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች የጥቃት ሰለባ ሆነዋል ። ግጭቱ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶም ለምዕራብ ሰሀራ ውዝግብ መፍትሄ ለመሻት በርካታ ጥረቶች ቢደረጉም ከአንዱ በስተቀር አብዛኛዎቹ ውጤት አላስገኙም ። ከእስካሁኖቹ ጥረቶች አንድ ውጤት ያመጣው እአአ በሺህ ዘጠኝ መቶ ዘጠና አንድ በተባበሩት መንግስታ ድርጅት አማካይነት የተካሄደው ድርድር ነው ። በዚሁ ድርድር የምዕራብ ሰሀራ ጉዳይ በህዝበ ውሳኔ እንዲፈታ ስምምነት ላይ ተደርሷል ። ይሁንና ይህ ስምምነትም ቢሆን እንከን አላጣውም ። ሁለቱ ወገኖች እስካሁን በህዝበ ውሳኔው መሳተፍ ያለበት ማን ነው በሚለው ነጥብ ላይ መግባባት አልቻሉም ። የመንግስታቱ ድርጅት ማን ነው ህዝበ ውሳኔ መስጠት ያለበት ለሚለው ግልፅ ነገር ባለማስፈሩ ጉዳዩ አሁንም በዕንጥልጥል ላይ ነው ። ከፖሊሳርዮ ነፃ አውጭ ንቅናቄ መስራቾች አንዱ የሆኑት ባሽር ኤዳልቺል
ድምፅ
“የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ህዝበ ውሳኔ መስጠት የሚገባውን መራጭ በግልፅ አላሳወቀም ። ስራውን ጀምሮታል ። ነገር ግን በህዝበ ውሳኔው የመሳተፍ መብት ያላቸው ሰሀራውያን የትኞቹ እንደሆኑ ግን አልወሰነም “
ይህ አንዱ ችግር ሲሆን ሞሮኮም አሁን ህዝበ ውሳኔውን በመቃወም ምዕራብ ሰሀራ በሞሮኮ ግዛት ስር አንድ ራስ ገዝ እንድትሆን ለፀጥታ ጥበቃው ምክርቤት ሀሳብ አቅርባለች ።ይህን ሀሳብ ደግሞ ፖሊሳርዮ አይቀበልም ። በዚህ ደረጃ ላይ የሚገኘው የሁለቱ ወገኖች አቋም የሚታረቅ ባይመስልም ዛሬ ኒውዮርክ ውስጥ የሚካሂዱት ድርድር አዲስ ተስፋ ይፈነጥቅ ይሆናል የሚል ዕምነት ተጥሎበታል ።

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW