የሥራ እድል ለሳዑዲ ተመላሾች
ሐሙስ፣ ሰኔ 8 2009በሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የህዝብ ግኑኝነትና የኮሙኒኬሼን ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ግርማ ሸለመ ብሔራዊ አስመላሽ ኮሚቴ ግብረሃይል ወደ ሳዑዲ በሚገኘዉ ኤምባሲና፣ በቆንሱላ ጽሕፈት ቤት ሰባት ማዕከላት ተቋቁሞ ዜጎቹ እዛ መጥተዉ እንሲመዘገቡ እያደረጉ እንደሚገኙ ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል።
ይሁን እንጅ እስካሁን ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ የጉዞ ሰነድን ወስደዋል የተባሉት ዜጎች ከ50,000 በላይ ቢሆኑም ቀሪዎቹ አሁንም ወደ ኢትዮጵያ ላለመመለስ ፖለቲካዊም ሆነ ኢኮኖሚያዊ ምክንያቶችን ማቅረባቸዉ ነዉ የሚነገረዉ። የኢትዮጵያ መንግስት ዜጎቹ ወደ አገራቸዉ ሲመለሱ የሥራ እድል እንደሚፈጥርላቸዉ በተደጋጋሚ ገልፀዋል።
ዜጎቹን ለማጓጓዝ የኢትዮጵያ አያር መንገድ የትኬት ዋጋን ቀደም ሲል 180,000 ሪያል ያወጣ የነበረዉ አሁን በመቀነስ 90,000 ሪያል እንዳደረገና 21 እቃዎችን በቀረጥ ነፃ እንድያስገቡ ማደረጉን አቶ ግርማ ተናግረዋል።
በሳዑዲም ሆነ በአገር ዉስጥ ያሉ ይህን የመንግስት የሥራ ፈጠራ እቅድ በጥርጣሬ የሚመለከቱት አልጠፉም። የኢትዮጵያ መንግስት የሥራ ፈጠራ እቅድ እንዴት ትመለከቱታለችሁ ብለን አስተያየት ጠይቀንም ነበር።
የአባት ስማቸዉን ያልጠቀሱት ከሳዑዲ መመለሳቸዉን የተናገሩት አቶ ታጠቅ መንግሥስት በፖለቲካ አቋማቸዉ በጥቃቅንና አነስተኛ እንዲደራጁ ሲጠየቁ እንዳልተቀበሉት በዶይቼ ቬሌ ዋትሳፕ ላይ የድምፅ መልክት ልከዉልናል።
አገር ዉስጥ ላሉትም ዜጎች መንግሥት የሥራ እድል እፈጥራለሁ የሚለዉ «ወሬ» ብቻ ነዉ፣ አሁን ለሳዑዲ ተመላሾች እየተገባ ያለዉ ቃልም ተመሳሳይ ነዉ የሚል አስተያየት አብዛኞች ተከታታዮቻችን ልከዉልናል።ወደ አምስት ዓመት ሳዑዲ አራብያ መቀመጣቸዉን የተናገሩት ግን ስማቸዉ እንዳይጠቀስ የጠየቁን ሌላዉ አስተያየት ሰጭ መንግስት በቅርቡ ይፋ ያደረገዉ የ10 ቢሊዮን ብር የሥራ እድል ፈጠራ እቅድ የት ገባ ሲሉ ጠይቀዋል።
በ2006 ዓ.ም የሳዑዲ መንግስት በሃገሪቱ የነበሩና ሕገወጥ ያላቸዉን ወደ 250,000 የሚሆኑ የተለያዩ አገር ዜጎች ከአገሩ ማስወጣቱ ይታወሳል። ከዚህም ዉስጥ ከ 160,000 በላይ የሚሆኑት ኢትዮጵያዉያን ነበሩ።
መርጋ ዮናስ
አዘብ ታደሰ