የሩስያዉ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር በአዲስ አበባ
ማክሰኞ፣ ሐምሌ 19 2014
የሩስያዉ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ላቭሮቭ አዲስ አበባ ገቡ። ላቭሮቭ በአዲስ አበባ ቆይታቸዉ ከኢትዮጵያና ከአፍሪቃ ህብረት ባለሥልጣናት ጋር ይገናኛሉ ተብሎ ይጠበቃል። የላቭሮቭ የአፍሪቃ ሃገራት ጉብኝት ዓላማ የሩስያ ዩክሬንን ወረራ ተከትሎ ሩስያን ለማውገዝ ከምዕራባውያን ጎን ያልቆመውን የአፍሪቃን ክፍለ ዓለምና የሩስያን ግንኙነት ማጠናክር ነው። ከምዕራቡ ዓለምና ከቀድሞዋ ሶቭየት ኅብረት ጋር ጥብቅ ግንኑነት ካላቸው የአፍሪቃ ሃገራት አብዛኛዎቹ በዩክሬኑ ጦርነት ገለልተኛ አቋም ነው የያዙት። በርካታ የአፍሪቃ ሃገራት ከሩሲያና ከዩክሬይን ስንዴና ሌሎች እህሎች ላይ ጥገኛ ናቸው። በሩስያ ዩክሬይን ጦርነት ምክንያት አፍሪቃ ሃገራት ከዩክሬይን የሚገዙት እህል በመስተጓጎሉ የረሃብ አደጋውን ሊያባብሰው እንደሚችል የተመድ በቅርቡ አስታውቋል።
የሩስያዉ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር አገራቸዉ ሩስያ በተባበሩት መንግሥታት ፀጥታዉ ምክር ቤት አፍሪቃን ጨምሮ ታዳጊ ሃገራት በሙሉ የበለጠ ሚና እንዲኖራቸዉ ምክር ቤቱን ለማሻሻል የሚደረገዉን ጥረት እንደምትደግፍ አስታወቁ። ባለፈዉ እሑድ የአፍሪቃ ጉብኝታቸዉን ከግብጽ የጀመሩት ላቭሮቭ ይህን የተናገሩት ዛሬ የኮንጎ ጉብኝታቸዉን አጠቃለዉ የዮጋንዳ ጉብኝታቸዉን ሲጀምሩ ነዉ። ላቭሮቭን በኢንቴቤ ዓለም አቀፍ አዉሮፕላን ጣብያ ተገኝተዉ አቀባበል ያደረጉላቸዉ የዩጋንዳው አቻቸው ጄጄ ኦዶንጎ ናቸው። የሩስያዉ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌይ ላቭሮቭ የዩጋንዳዉ ፕሬዚዳንት ዩዌሪ ሙሰቪኒ ጋርም ተገናኝተዋል። ላቭሮቭ ከኮንጎ ወደ ዩጋንዳ ከማቅናታቸዉ በፊት ከኮንጎው ፕሬዝዳንት ዴኒስ ሳሱ ንጋሶ እና ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዣን ክሎድ ጋኮሶ ጋር ተገናኝተዋል። አንድ የሩስያ ከፍተኛ ዲፕሎማት ኮንጎን ሲጎበኝ ላቭሮቭ የመጀመሪያው ናቸው።
አዜብ ታደሰ
ሸዋዬ ለገሰ