የርዕሰ-ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንሲስ ግብዓተ-መሬት በሮማ ከተማ በቅድስት ማርያም ካቴድራል ተፈጸመ
ቅዳሜ፣ ሚያዝያ 18 2017
የሮማ ካቶሊካዊት ቤተ-ክርስቲያን ርዕሰ-ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንሲስ ግብዓተ-መሬት ዛሬ ቅዳሜ በጣልያን ሮማ ከተማ በምትገኘው ቅድስት ማርያም ካቴድራል ተፈጽሟል። ፍራንሲስ ከጎርጎሮሳዊው 1903 በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ከቫቲካን ውጪ የተቀበሩ የቤተ-ክርስቲያኒቱ ርዕሰ-ሊቃነ ጳጳስ ሆነዋል።
አርጀንቲናዊው ፍራንሲስ ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት በ88 ዓመታቸው ነበር። በፍራንሲስ ምትክ የሮማ ካቶሊካዊት ቤተ-ክርስቲያን በእጅግ ሚስጥራዊ ሒደት አዲስ ርዕሰ-ሊቃነ ጳጳሳት ትመርጣለች። በምርጫው አፍሪካን ጨምሮ ከተለያዩ የዓለም ክፍሎች የተውጣጡ ጳጳሳት ይሳተፋሉ።
ርዕሰ-ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንሲስ ግብዓተ-መሬት የተፈጸመው በቫቲካን ቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ስንብት ከተደረገላቸው በኋላ ነው። የጀርመን መራኄ መንግሥት ኦላፍ ሾልስ፣ የአሜሪካ ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ፣ የፈረንሳይ ፕሬዝደንት ኤማኑዌል ማክሮ፣ የዩክሬን ፕሬዝደንት ቮሎዶሚር ዜሌንስኪ እና የብሪታኒያ ጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታራመርን ጨምሮ የበርካታ ሀገራት መሪዎች ተገኝተዋል።
ቢያንስ 400,000 ሰዎች በቫቲካን እና በመንገድ ላይ በመሰለፍ ስንብታቸውን እንደታደሙ የጣልያን የሀገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር ማቴዎ ፒያንቴዶሲ ተናግረዋል።
በቅዱስ ፔጥሮስ አደባባይ እና በአካባቢው ብቻ 250,000 ሰዎች መገኘታቸውን ቫቲካን አስታውቃለች።
በሮም ከተማ አውራ ጎዳናዎች ተሰልፈው የርዕሰ-ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንሲስ ወደ መጨረሻው ማረፊያ ሥፍራ ሲጓዝ 150,000 ሰዎች ተከታትለዋል ተብሏል።
ርዕሰ-ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንሲስ በተናዘዙት መሰረት ግብዓተ-መሬታቸው በመሀል ሮም በምትገኘው በቅድስት ድንግል ማርያም ካቴድራል ተፈጽሟል። ቤተ-ክርስቲያኒቱ ከቅዱስ ጴጥሮስ ካቴድራል በስድስት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ እንደምትገኝ በሮም የቀድሞው የዶይቼ ቬለ ዘጋቢ ተክለእዝጊ ገብረየሱስ ተናግሯል።
አስከሬናቸው በጳጳሳት፣ በካሕናት እና በሕዝብ ታጅቦ ወደ ቅድስት ድንግል ማርያም ካቴድራል ተወስዷል። የርዕሰ-ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንሲስ ግብዓተ-መሬት የሚርቧቸው ብቻ በተገኙበት መፈጸሙን ቫቲካን አስታውቃለች።
ተክለእዝጊ ገብረየሱስ
እሸቴ በቀለ