1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሶማሊያ የሰላም ንግግር

ረቡዕ፣ ሐምሌ 12 1998

የሶማሊያ የሽግግር መንግስት ፕሬዝዳንት አብዱላሂ ዩሱፍ

ምስል AP

የሶማሊያ የሽግግር መንግስት አብዛኛውን የሶማሊያ ደቡባዊ ክፍል ከተቆጣጠረው የሸሪያ ፍርድ ቤቶች ህብረት ጋር ለመነጋገር ተስማማ ። በአሁኑ ሰዓት በእጅጉ የተዳከመው የሽግግር መንግስቱ በዕርቀ ሰላሙ ንግግር ለመሳተፍ የተስማማው በዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ ግፊት መሆኑን የሽግግር መንግስቱ ቃል አቀባይ አብዱራህማን ሞሀመድ ዲናሪ አስታውቀዋል ። በቅርቡ ሞቃዲሾን ከተቆጠረ በህዋላ ይዞታውን ያስፋፋው የሸሪዓ ፍርድቤቶች ህብረት የህዝቡ ድጋፍ ቢኖረውም በውጭው ዓለም ዘንድ ግን በጥርጣሬ ነው የሚታየው ። የቀድሞው የሶማሊያ መሪ ዚያድ ባሬ ከስልጣን ከወረዱ ከዛሬ አስራ አምስት ዓመት ወዲህ በሶማሊያ ብጥብጥ ረሀብ ሽብር እና ጥፋት ነው ሰፍኖ የቆየው ። ዋና ከተማይቱ ሞቃዲሾም ከባግዳድ ቀጥሎ በዓለማችን አደገኛ ከሚባሉት ከተሞች አንድዋ ናት ። እአአ ከሺህ ዘጠኝ መቶ ዘጠና አንድ አንስቶ ሞቃዲሾን ሲቆጣጠሩ የቆዩት የጦር አበጋዞች ባለፈው ወር በሸሪዓ ፍርድቤቶች ህብረት ተሸንፈው ከተማይቱን ለቀው ወጥተዋል ። በጦር አበጋዞቹ ዘመን ህዝቡ በፍርሀትና በጭንቀት ነበር የሚኖረው ። ህብረቱ ሞቃዲሾን ከተቆጣጠረ ወዲህ ግን ሁኔታው ተቀይሮዋል ። በከተማይቱ ፀጥታ ሰፍኖዋል ። ለዚህም ህዝቡ ትልቅ ግምት ሰጥቶታል ። በዚህ ባልተጠበቀ ሁኔታ ሙስሊም ሚሊሽያዎቹ በሶማሊያ ሰላም የማያመጡ ነው የሚመስለው ። ከዚህ ቀድም ሰላም በሶማሊያ ትርጉም የለሽ ተደርጎ ነበር የሚወሰደው ። አሁን ግን የሰላም ተስፋ ይታያል ። ሆኖም ግን አሁንም ቢሆን በሞቃዲሾ መቶ በመቶ ፀጥታ ሰፍኖዋል ማለት አይቻልም ። በኬንያ የሶማሊያ አምባሳደር ሞሀመድ አፌይ
“በሞቃዲሾ በአጠቃላይ የፀጥታው ሁኔታ ፍፁም አይደለም ። እንደምታውቁት በዋና ከተማይቱ በሞቃዲሾ መቶ በመቶ ፀጥታ አለ ብለን ማረጋገጥ አንችልም ።ነገርግን እንደሚመስለኝ የሶማሊያ ህዝብ ውይይት እንዲደረግ ቁርጠኝነቱን አሳይቶዋል ። ሁሉም የፍርድቤቱ ህብረት አባላት አይደሉም ። ሆኖም ህብረቱ የህዝቡ ፣ የሲቪል ማህበራት ፣ የንግዱ ማህበረሰብና የባህላዊ መሪዎች ከፍተኛ ድጋፍ አለው ። ሁሉም ፀጥታና መረጋጋት ስለሚፈልጉ አንድ ሆነዋል ። “
የሸሪዓ ፍርድቤቶች ህብረት በራሳቸው የቆሙ አክራሪ የሀይማኖት መሪዎችንና ነጋዴዎችን ያቀፈ ነው ። ህብረቱ በዩናይትድ ስቴትስ የሽብርተኝነት መፈልፈያ ተደርጎ ነው የሚወሰደው ። ከዋና ከተማይቱ ከሞቃዲሾ ሁለት መቶ ሀምሳ ኪሎሜትር ርቀት ላይ የሚገኘው የተዳከመው የሶማሊያ የሽግግር መንግስት ህብረቱን በይፋ እንደ ተደራዳሪ አይቀበለውም ።ይሁንና የሽግግር መንግስቱ አሁን ከህብረቱ ጋራ ለመደራደር ተስማምቶዋል ። የሶማሊያው ጠቅላይ ሚኒስትር አሊ ሞሀመድ ጌዲ
“ ለሸሪዓ ፍርድቤቶች ህብረት ዕውቅና እንሰጣለን ። ሆኖም ግን ከአልቃይዳና ከሽብርተኞች ጋር ግንኙነት ካላቸው አክራሪዎች ጋር አንደራደርም ። ከሼህ አዌይስ ጋር መደራደር ማለት ከቢን ላደንና ከአጋሩ ከአልቄይዳ ጋር መነጋገር ማለት ነው ። “

የህብረቱ መሪ ሀሰን ዳሂር አዌይስ ሶማሊያን ለአፍሪቃ የቀንደኛ ሽብርተኞች ማገናኛ ድልድይ ያደርግዋትዋል ተብለው በሶማሊያ የሽግግር መንግስትና በዩናይትድ ስቴትስ ይጠረጠራሉ ። ይሁና የዚህ ጥርጣሬ ማረጋገጫ ግን እስካሁን አልተገኘም ። ህዝቡ ደግሞ ከደካማው የሽግግር መስግስት ሚሊሽያዎቹን ነው ያመነው ። በዚህ የተነሳም የሽግግር መንግስቱ ለመግባባት ራሱን ማዘጋጀት እንዳለበት ነው የሚታመነው ። ከዚህ አንፃር ይመስላል የሽግግር መንግስቱ ፕሬዝዳንት አብዱላሂ ዩሱፍ ከዚህ ቀደም የተቃወሙትን የድርድር ሀሳብ እንደገና ተቀብለውታል ።
የሶማሊያው ጠቅላይ ሚኒስትር አሊ ሞሀመድ ጌዲ

“ከሸሪዓ ፍርድቤት አባላት ጋር እንገናኛለን ። ሆኖም ግን ባለፉት ጥቂት ሳምንታት የተኩስ አቁም ስምምነቱን ከጣሱት በሞቃዲሾ የርስ በርሱ ጦርነት የዘር ማጥፋት ወንጀል ከፈፀሙትና ንብረት ካወደሙት ጋር ግን አብረን አንቀመጥም ። “

ወደፊት የታሰበው የሰላም ንግግር በትክክል ተሳክቶ ከተካሄደ ከዓመታት በህዋላ በሶማሊያ ሰላም የመስፈኑን ተስፋ አሳድሮዋል ። ይህ ካልሆነ ግን ሀገሪቱ በሞላ ጦርነት ያሰጋታል ።

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW