የሶማሌ ክልል ዋና ከተማ ጅግጅጋ ነዋሪዎች ስለ ምርጫ ምን ይላሉ?
እሑድ፣ ግንቦት 23 2018
ነገ ለሚካሄደው 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ድምፅ ለመስጠት መዘጋጀታቸውን ለዶይቼ ቬለ አስተያየት የሰጡ የጅግጅጋ ነዋሪዎች ገልፀዋል። በሀገሪቱ በ1997 የተካሄደውን ሀገራዊ ምርጫ በበጎ የሚያስታውሱት የጅግጅጋ ነዋሪው አቶ ጉተማ ዘውዴ በበኩላቸው አስቻይ ሁኔታ ኖሮ ሳይሆን ወቅቱን መጠበቅ ግድ ስለሆነ የተካሄደ ነው ብለዋል።
ለመራጭነት የሚያበቃውን ካርድ የወሰደ ማንኛውም ሰው የሚጠቅመውን አስቦ መምረጥ እንዳለበት የሚናገረው የጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲው መምህር ሱራፌል መኩርያ መምረጥ ስልጣን ከሚረከበው አካል ጋር አብሮ መስራት ማለት እንደሆን ገልፃል። አስተያየት ሰጭዎቹ መምረጥ ካለመምረጥ የተሻለ መሆኑን ሀሳባቸውን አጋርተዋል።
የሶማሌ ክልል በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ላሉት 23 መቀመጫዎች ገዢው ብልፅግና ፓርቲን ጨምሮ የ12 የፖለቲካ ፓርቲዎች ዕጩዎች እና አራት የግል ተወዳዳሪዎች ለምርጫ ቀርበዋል።
ለክልሉ ምክር ቤት መቀመጫዎች የሚወዳደሩት 12 የፖለቲካ ፓርቲዎች ዕጩዎች እና 39 የግል ተወዳዳሪዎች ናቸው። የሶማሌ ክልል ምክር ቤት 273 መቀመጫዎች አሉት።
ለሰባተኛው የኢትዮጵያ ጠቅላላ ምርጫ ለክልል ምክር ቤት መቀመጫዎች ከሚወዳደሩት መካከል ነፃነትና እኩልነት ፓርቲ፣ የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃነት ግንባር፣ የምዕራብ ሶማሌ ዲሞክራቲክ ፓርቲ እና ኅብረት ለዲሞክራሲና ለነፃነት ፓርቲ ይገኙበታል። በግል የሚወዳደሩ 39 ዕጩዎችም ቀርበዋል። የሶማሌ ክልል ብዛት ያላቸው የግል ተወዳዳሪዎች በማስመዝገብ ከተቀሩት ክልሎች እና የከተማ አስተዳደሮች ከፍተኛ ብልጫ አለው።
መሳይ ተክሉ
እሸቴ በቀለ