የሶርያ ውዝግብና የዓለም ሀገሮች
ረቡዕ፣ ግንቦት 22 2004 በመቃወም ጀርመን፡ ፈረንሣይና በርካታ የአውሮጳ ህብረት ሀገሮች፡ እንዲሁም፡ ዩኤስ አሜሪካ፡ ካናዳ፡ አውስትሬሊያ፡ ቱርክና ጃፓን የሶርያ አምባሳደሮችና ከፍተኛ ዲፕሎማቶች በሰባ ሁለት ሰዓት ሀገሮቻቸውን ለቀው እንዲወጡ አዘዋል። የዶይቸ ቬለ ባልደረባ ኡልሪኽ ላይድሆልት እንደሚለው፡ ምዕራባውያቱ ሀገሮች ይኸው ያጠናከሩት ግፊት የአሳድ መንግሥት በተቃዋሚዎች ላይ እየወሰደ ያለውን የኃይል ርምጃ እንዲያበቃ ማስቻሉን ብዙዎች ይጠራጠሩታል።
ትናንት በደማስቆ ከሶርያ ፕሬዚደንት በሺር ኧል አሳድ ጋ የተወያዩት የሶርያ ልዩ ልዑክ ኮፊ አናን የሶርያ መንግሥት ደም አፋሳሹን ግጭት አሁኑኑ እንዲያበቃ እና አሳድም ውዝግቡን ለማብቃት አናን ያዘጋጁትን ባለስድስት ነጥብ የሰላም ዕቅድ ተግባራዊ የማድረጉን ቆራጥ ርምጃ ነገ ሳይሆን ዛሬውኑ እንዲወስዱ አሳስበዋል። በውዝግቡ የሚፋለሙት የጦር ኃይሉና ተፋላሚ ሚሊሺያዎችም በጠቅላላ የኃይሉን ርምጃ እንዲያቆሙና የሰላሙን ዕቅድ እውን ለማድረግ የሚጠበቅባቸውን ድርሻ እንዲያበረክቱ በጥብቅ ጠይቀዋል። ይሁንና፡ በሁላ ከመቶ የሚበልጥ ሰው የተጨፈጨፈበት ድርጊት ግን ለሶርያ ውዝግብ በድርድር መፍትሔ ማገኘቱ ምን ያህል አዳጋች መሆኑን እንዳሳየ አናን ተገንዝበውታል።
« ይህ የሰላም መልዕክት ለመንግሥቱ ብቻ ሳይሆን፡ የጦር መሣሪያ ለያዛ ማንኛውም ግለሰብ ነው። ባለ ስድስት ነጥቡ አጠቃላይ የሰላም ዕቅድ ተግባራዊ መሆን አለበት። ግን ዛሬ ይህ እየሆነ አይደለም። »
በሰላሙ ዕቅድ መሠረት የተኩስ አቁሙ ደንብ ካለፉት ሰባት ሣምንታት ወዲህ ተግባራዊ ነው ቢባልም እና የተመድ ታዛቢ ቡድን በሀገሪቱ ቢሰማራም፡ በሶርያ ግድያው አላበቃም። በዚህም የተነሳ ጀርመን፡ ፈረንሣይና በርካታ የአውሮጳ ህብረት ሀገሮች፡ እንዲሁም፡ ዩኤስ አሜሪካ፡ ካናዳ፡ አውስትሬሊያ፡ ቱርክና ጃፓን የሶርያ አምባሳደሮችና ከፍተኛ ዲፕሎማቶች ሀገሮቻቸውን ለቀው እንዲወቱ የሰባ ሁለት ሰዓት ጊዜ ሰጥተዋል። የሁላውን ዓይነት ግድያ ለማብቃት በሶርያ አንፃር ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ እስከተስማማ ድረስ ወታደራዊ ርምጃ አይወሰድም ተብሎ እንደማይታሰብ የፈረንሣይ ፕሬዚደንት ፍራንስዋ ኦሎንድ አስታውቀዋል።
« ወታደራዊው ርምጃ ከጥያቄ ውጭ አይደለም። ዓለም አቀፉ ሕግ እስከተከበረ ድረስ። ማለትም የተመድ ፀጥታ ጥበቃ ምክር ቤት ከመከረ በኋላ መሆን ይኖርበታል። እኔና ሌሎች ሩስያውያኑንና ቻይናውያኑን ማግባባት፡ እንዲሁም፡ መፍትሔ ማፈላለግ ይጠበቅብናል። ይህ መፍትሔ የግድ ወታደራዊ ርምጃ መሆን የለበትም። ግን የበሺር ኧል አሳድን መንግሥት ለማስወገድ በወቅቱ ግፊቱ መጠናከር ይኖርበታል። »
ምክር ቤቱ ወታደራዊ ርምጃ የሚወሰድበትን ውሳኔ ማሳለፍ ይችል ዘንድ ግን ሩስያ እና ቻይና ዕቅዱን እንዲደግፉ ማግባባት አስፈላጊ መሆኑን ኦሎንድ አመልክተዋል።
ይሁንና፡ ቻይና እና ሩስያ ምንም እንኳን የፀጥታ ጥበቃ ምክር ቤቱ የሁላን ግድያ ያወገዘበትን ውሳኔ ቢደግፉም፡ በሶርያ አንፃር ማንኛውንም ወታደራዊ ርምጃ እንደማይደግፉ ግልፅ አድርገዋል። ይህ ዓይነቱ ውሳኔ ውዝግቡን ይበልጡን እንደሚያባብሰው የሩስያ ውጭ ጉዳይ ሚንስትእር ሴርጌይ ላቭሮቭ ገልጸዋል።
« በምንወስደው ማንኛውም ርምጃ ላይ በጣም ጥንቃቄ ማድረግ ይገባናል። እሣት ላይ ነዳጅ ማርከፍከፍ የለብንም። በዚህ ፈንታ ውዝግቡን ማብረድና ተቀናቃኞቹን ወገኖች እንደገና ወደ ድርድሩ ጠረጴዛ እንዲመለሱ ማድረግ ይጠበቅብናል። »
በኃይል የሚደረግ የሥልጣን ለውጥን በጥብቅ እንደምትቃወምም ቻይና በተጨማሪ አስታውቃለች።
ልክ እንደቻይናና ሩስያም የዐረብ ሊግ አባል ሀገሮች ወታደራዊ ርምጃን አይደግፉም። እስካሁን አንድም የሶርያን ዲፕሎማት ከሀገራቸው አላስወጡም።
በሶርያ ግድያው እንዳይቀጥል ለማከላከል ዲፕሎማቲኩን ግፊት ከማጠናከር የተሻለ ሌላ አማራጭ እንደሌለ ነው የገለጹት።
አርያም ተክሌ
ሂሩት መለሰ