የሽብር ስጋት በብራስልስ
ቅዳሜ፣ ኅዳር 11 2008ማስታወቂያ
የባቡር አገልግሎት ሙሉ በሙሉ የተቋረጠ ሲሆን የከተማዋ የጸጥታ ጥበቃ ከፍተኛ ከሚባለው ደረጃ እንዲደርስ ተደርጓል። የቤልጅየም ጠቅላይ ሚኒስትር ቻርለስ ሚሼል «አደጋው ግልጽና ተጨባጭ ለመሆኑ በቂ መረጃ አለን።» ሲሉ ተናግረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጥቃቱ በርካታ ሰዎችና የጦር መሳሪያዎች የሚያሳትፍ ምን አልባትም እንደ ፓሪስ ሁሉ በተለያዩ ቦታዎች በተመሳሳይ ሰዓት ሊደረግ የታቀደ መሆኑን ጨምረው አስረድተዋል። በርካታ ሰዎች የሚሰበሰቡባቸው የሙዚቃ ዝግጅቶች፤የአደባባይ መሰናዶዎች እና ስፖርታዊ ውድድሮች በሙሉ እንዲሰረዙ ትዕዛዝ ተላልፏል። «ስጋቱ አደገኛ ነው።» ያሉት የቤልጅየም አገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር ዣን ዣምቦ በቁጥጥራቸው ስር እንደሆነ ተናግረዋል። ከፓሪስ ጥቃት ፈጻሚዎች መካከል አብዛኞቹ የአውሮጳ ህብረትና የስሜን ቃል-ኪዳን የጦር ትብብር (NATO) መቀመጫ ከሆነችው የብራስልስ ከተማ ጋር ግንኙነት ነበራቸው።
እሸቴ በቀለ
አዜብ ታደሰ