የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በቀረቡባቸው ክሶች ጥፋተኛ ተባሉ
ዓርብ፣ ግንቦት 23 2016
የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በኒውዮርክ ውስጥ በቀረቡባቸው 34 የክስ መዝገቦች ሙሉ በሙሉ ጥፋተኛ ተባሉ። ይሄው የጥፋተኝነት ውሳኔ የተሰጠው ከዚህ ቀደም ያሸነፉበት ምርጫ ላይ ከትዳራቸው ውጪ የነበራቸው ግንኙነት እንዳይታወቅ አፍ ማስያዥያ ገንዘብ በመስጠትና፣ የተጭበረበረ የሂሳብ ሰነድ ከማዘጋጀት ጋ በተያያዘ በቀረቡባቸው ክስ ነው። ዶናልድ ክሱንም ውሳኔውንም ህገወጥና አሳፋሪ ብለውታል። ደውቸ ወለ ያነጋገራቸው የህግ ባለሞያ ትራምፕ ቢፈረድባቸውም ለምርጫ ከመወዳደር የሚያግዳችሀው ህግ እንደሌለ ጠቁመዋል።የዶናልድ ትራምፕ የምርጫ ተሳትፎ በፍርድ ቤት ሊታይ ነው
ጥፋተኛ ናቸው የሚለው ቃል ለቀረቡባቸው 34 ክሶች፤ 34 ጊዜ ተጠርቷል። ከዚህ ቀደም ሆኖ በማያውቅ ሁኔታ የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት፣ የአሁኑ የሪፐብሊካን ፓርቲ የፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ተፎካካሪ፤ በሁሉም ክሶች ጥፋተኛ ተብለዋል። ኒውዮርክ ውስጥ በዋለው ችሎት ጥፋተኛ የተባሉበት ክስ ያሸነፉበት ያለፈው ምርጫ ሲቃረብ፣ ከትዳራቸው ውጪ ማግጠዋል ከተባሉባት ስቶርሚ ዳንኤል ከተባለች ግለሰብ ጋር የነበራቸው ግንኙነት ለመደበቅ ለግለሰቧ አፍ ማዘግያ ይሆን ዘንድ ክፍያ መፈጸማቸውን ተከትሎ፤ በምርጫ ውጤቱ ላይ ጫና እንዳያሳድርባቸው ክፍያ መፈፀሙን ለመደበቅ የሃሰት ሰነዶችን መጠቀማቸው ጋር የተያያዙ ናቸው።
ክሱን ያቀረቡትና የመሩት የማንሃተን ክፍለ ከተማ ጠቅላይ አቃቢ አልቪን ብራግ ከጥፋተኝነት ውሳኔው በኋላ እዚህ ክስና ፍርድ ላይ የደረስነው ያለምንም ፍርሃትና ጥቅመኝነት ህጉንና እውነትን ተከትለን ነው ብለዋል። በርካታ ያልተዘጉ የክስ መዝግቦች የተደቀኑባቸው ዶናልድ ትራምፕ ግን ይሄ የጥፋተኝነት ውሳኔ አሳፋሪ ተግባር፣ ጠቅላላ ክሱም የፖለቲካ ጫና ነው ብለዋል።
ክሱ በእስር የሚያስቀጣ ቢሆንም፣ ዳኛው የተለያዩ አማራጮችን ከግምት ውስጥ ሊያስገቡ እንደሚችሉ ያነጋገርኳቸው የህግ ባለሙያና ጠበቃ ዶክተር ፍጹም አቻሜለህ አለሙ ጠቁመዋል። ዶናልድ ትራምፕ ላይ የቅጣት ውሳኔ በሚሰጥበት ሐምሌ ወር ውስጥ የሪፐብሊካን ፓርቲ በይፋ እጩነታቸውን ሊያበስር ቀጠሮ ይዟል። በዚሁ ፍርድ ቤት እስራት ቢፈረድባቸውም እንኳን ለፕሬዘዳንትነት ከ መወዳደር የሚያግዳቸው ነገር እንደሌለ የህግ ባለሙያው ዶክተር ፍጹም አለሙ ገልጸዋል።የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ዘመቻ
አሁንም ድረስ የማይናወጥ የደጋፊ መሠረት ያላቸው ዶናልድ ትራምፕ 80 በመቶ የሚሆኑት ደጋፊዎቻቸው ቢታሰሩም ድጋፋቸውን እንደሚቀጥሉ ተመልክቷል። የሪፐብሊካን ፓርቲ መሪዎችና የህዝብ እንደራሴወች በዶናልድ ትራምፕ ጥፋተኛ መባል ቁጣና ተቃውሟቸውን አሰምተውል። ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን በበኩላቸው ዶናልድ ትራምፕን ኋይት ሃውስ ደጅ እንዳይደርስ ለማድረግ ብቸኛው አማራጭ በምርጫ ኮሮጆ መጣል ነው ብለዋል። ዶናልድ ትራምፕ መጨረሻቸው እስርቤትም ይሁን ኋይት ሃውስ፤ የዚህ የፍርድ ሂደት፣ ማንም ሰው የትኛውም ሀይልና ስልጣን ቢኖረው ከህግ በላይ አይደለም።
ሙሉ ዝግጅቱን የድምፅ ማዕቀፉን ተጭነው ያድምጡ።
አበበ ፈለቀ
ፀሀይ ጫኔ
እሸቴ በቀለ