1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የቀድሞ አባገዳ አጋ ጠንጠኖ ፋውንዴሽን ምስረታ

ማክሰኞ፣ ኅዳር 18 2016

ባለፈው 2015 ዓ.ም. ሕይወታቸው ባለፈው በአባገዳ አጋ ጠንጠኖ ስም የተመሰረተው ፋውንዴሽን ተመሰረተ ። ፋውንዴሽኑ የተመሰረተው የገዳ ሥርዓት ማስቀጠል ዋና ዓላማ አድርጎ መሆኑም ተገልጿል ። ፋውንዴሽኑ እሁድ ኅዳር 23 ቀን 2016 ዓ.ም. በይፋ ይተዋወቃልም ተብሏል ።

በአባገዳ አጋ ጠንጠኖ ስም የተመሰረተው ፋውንዴሽን
በአባገዳ አጋ ጠንጠኖ ስም የተመሰረተው ፋውንዴሽን ይፋ ሲደረግምስል Seyoum Getu/DW

በ72ኛው የጉጂ አባገዳ ስም የተመሰረተው ፋውንዴሽን

This browser does not support the audio element.

ባለፈው 2015 ዓ.ም. ሕይወታቸው ባለፈው በአባገዳ አጋ ጠንጠኖ ስም የተመሰረተው ፋውንዴሽን ተመሰረተ ።  ፋውንዴሽኑ የተመሰረተው የገዳ ሥርዓት ማስቀጠል ዋና ዓላማ አድርጎ መሆኑም ተገልጧል ። ፋውንዴሽኑ እሁድ ኅዳር 23 ቀን 2016 ዓ.ም. በይፋ ይተዋወቃልም ተብሏል ። 

72ኛው የጉጂ አባገዳ በነበሩትና ባለፈው ዓመት ሕይወታቸው ባለፈው አባገዳ አጋጠንጠኖ ስም የተመሰረተውን ፋውንዴሽን በማስመልከት በዛሬው እለት አዲስ አበባ ውስጥ በፋውንዴሽኑ መስራቾች ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰጥቷል፡፡ በጋዜጣዊ መግለጫውም የአጋ ግለታሪክና በገዳው ስርዓት ስላበረከቱት አስተዋጽኦ ገለጻዎች ተሰጥቷል፡፡ ስለሰላም በሚያስተላልፉት መልእክቶች የሚታወቁትና የዚህ ፋውንዴሽን የቦርድ ሰብሳቢ የክቡር ዶ/ር ኃይሌ ገብሬ መግለጫውን ከሰጡት የፋውንዴሽኑ መስራቾች ተጠቃሽ ናቸው፡፡

ዶ/ር ኃይሌ በዚሁ መግለጫ ወቅት አጋ ጠንጠኖ በሕይወት እያሉ ታላቅ ሥራ የሠሩ ብለዋቸዋል፡፡ “ገዳ ከ600 ዓመታ በፊት ሕግ አውጥቶ ሕዝብ የመራ ስርዓት ነው፡፡ ከ19ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ ግን እየተሸረሸረ እስከመጥፋት የደረሰበት ጊዜ ነበር፡፡ አጋ ጠንጠኖ ግን ስልጣን ከተረከቡበት ጊዜ ጀምሮ ስርዓቱ እንዲንሰራራ እና እንዲያድግ አድርገዋል፡፡ ስለዚህ አጋ ማለት የገዳ ዳግም አዳሽ፤ በህይወታቸው ገዳን የተረጎሙ ሰው ነበሩ” ብለዋል፡፡

በስልጣን ዘመናቸው መንፈሳዊና ዓለማዊ መሪ የነበሩ የተባለላቸው አጋ ጠንጠኖ በስልጣን ዘመናቸው አገር በሙሉ አንድ እንዲሆን ሰላምና ፍቅርም እንዲሰፍን የሰሩ በሚልም ተሞካሽተዋል፡፡ “አጋ በኔ ስልጣን ዘመን ሁሉም ሰላም እንዲሆኑ ይሉ ነበር ። እሳቸው በመቶ ዓመት ጊዜ ውስጥ አንዴ እንዴ ሚፈጠር ሰው ናቸው፡፡”

በቀድሞ አባገዳ አጋ ጠንጠኖ ስም “ፋና አጋ” በሚል በተመሰረተው ፋንዴሽን ሊሰሩ የታቀዱ አበይት ጉዳዮችም ተዘርዝረዋል፡፡ “አንደኛው እሱ ያደረሰው ገዳ ስርዓት በምርምር እየበለጸገ ከምንደርስበት ማህበራዊ-ኢኮኖሚ ጋር እንዲያድግ ማድረግ ነው፡፡ ሁለተኛው አጋ እውነተኛ የህዝብ መሪ ስለነበሩ እንደሳቸው እራሳቸውን አሳልፈው የሚሰጡ የህዝብ መሪዎች እንዲፈጠሩ ማድረግ ነው፡፡ ሶስተኛው ገዳ እና ሃብቶቹ ለትውልድ እንዲተላለፉና የቱሪዝም መስእብ እንዲሆኑ ማደራጀት ነው፡፡ አራተኛው በስምንት ዓመት አንዴ እንደሱ ለሰላም ለሰሩ ሰዎች በስማቸው ሽልማት መስጠት ነው፡፡”

ኦሮሚያ ክልል ፤ መልክዓ ምድር በከልምስል Seyoum Getu/DW

የገዳ ስርዓትን ማስቀጠል ዋናው ዓለማ አድርጎ ተመሰረተ በተባለው በዚህ ፋውንዴሽን አገራዊ እሴቶች ለህዝቦች አንድነት እንዲያግዙም እንደሚሰራ ተጠቁሟል፡፡ “ገዳ በደንብ ከተጠና እኛ ኢትዮጵያውያን እሴት ያለን ህብረትያለን ህዝቦች ስለሚያደርገን በርብርብ መጠበቅ ገባናል፡፡ አጋራችን መልሰን ለመገንባትም የዴሞክራሲም ተምሳሌት ለማድረግ ይረዳናል፡፡ እሴት የሌለው ህዝብ ማንነት የሌለው ህዝብ ነው፡፡ የራሱን እሴት የጣለ ህዝብ የሌላውን እሴት ተሸካሚ ነው፡፡ ዛሬ የደረስንበት ፈተናም የዚሁ ማሳያ ነው፡፡”

የኦሮሞ የገዳ ስርዓት ጥልቅ የአስተዳደር እና መሪነት እሴት እንዳለው ይነገርለታል፡፡ ስርኣቱን የሚመሩ ሰዎችም በታሪኩ በጉልህ እንደሚከበሩ ይዳስሳል፡፡ ይሁንና ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የገዳ ስርዓቱ እና መሪዎቹ ተቀባይነት በመጠኑም ቢሆን አጠያይቋል፡፡ በዛሬው ጋዜጣዊ መግለጫም በዶይቼ ቬለ ስለጉዳዩ የተጠየቁት የፋውዴሽኑ መስራቾች በስርዓቱ እሴት ፋይዳ ላይ በመስራት የጣልነውን እሴታችንን ማንሳት የገጠመንን ጊዜያዊ ፈተና የሚያሳልፈን በመሆኑ የሚሰራበት ይሆናል ብለዋል፡፡

ሥዩም ጌቱ

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ነጋሽ መሐመድ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ከ DW