የቁሻሻ ክምር አደጋ ሠለቦች
ማክሰኞ፣ ግንቦት 22 2009ባለፈዉ መጋቢት መጀመሪያ በተደረሰመዉ የአዲስ አበባ ቁሻሻ ክምር ወዳጅ ዘመድ የሞቱባቸዉ እና የተፈናቀሉት አሁንም በቂ እርዳታ እንዳላገኙ አስታወቁ።የአዲስ አበባ መስተዳድር ለተፈናቃዮቹ የመጠለያ፤ የምግብ እና የቁሳቁስ ድጋፍ እንደሚያደርግ አስታዉቆ ነበር።በስልክ ያነጋገርናቸዉ ተፈናቃዮች እንደሚሉት ግን እስካሁን ድረስ የሚኖሩት በየዘመዱ ቤት አለያም በየግላቸዉ ተከራይተዉ ነዉ።ለቤቱ ኪራዩ መንግሥት ይደጉመናል ያሉ ሲኖሩ ሌሎቹ ግን የደረሰን እርዳታ የለም ባይ ናቸዉ።አደጋዉ የደረሰበት አካባቢ አሁንም ሌላ ቁሻሻ እየተከመረበት ነዉ።ነጋሽ መሐመድ ዝርዝር ዘገባ አለዉ።
በዚያ ሰሞን የፌደራልና የአዲስ አበባ መንግሥታት ባለሥልጣናት፤ የመንግሥትና ለመንግሥት ቅርበት ያላቸዉ መገናኛ ዘዴዎች አደጋ-ሐዘን፤ ርዳታ-የማፅናኛ ጉብኝት፤ መልሶ-ማቋቋም እያሉ አወሩ፤ አስወሩም።በአደጋዉ አንድ መቶ አስራ-አምስት ሰዎች መሞታቸ ተሰምቶ ነበር።የቆሰሉት ሥለ-መታከም፤ መረዳታቸዉ፤ የጠፉት ሥለ መገኘት-አለመገኛታቸዉ፤ የተቸገሩት ሥለ መረዳት አለመረዳታቸዉ በትክክል የተባለ ነገር የለም።ሰወስተኛ ወሩ አበቃ።
ባለፈዉ ሳምንት የአዲስ አበባ መስተዳድር ባለሥልጣናት መረጃ እንዲሰጡን ለመጠየቅ ከከንቲባዉ ቢሮ እስከ ሕዝብ ግንኙነቱ መስሪያ ቤት፤ ከቃል አቀባይዋ እስከ ሠራተኛና ማሕበራዊ ጉዳይ ቢሮ ደወልን።ገሚሶቹ ሥልክ አይመልሱም።ያነሱት እኛን አይመለከትንም አሉ።አዲስ አበባን ለደረሰ አደጋ ከአዲስ አበባ አስተዳዳሪዎች ሌላ ማንን ይሆን የሚመለከተዉ? «ምን ይሻላል ታዲያ» አሉኝ ያንዱ ቢሮ ባልደረባ እኔኑ መልሰዉ።
በአደጋዉ ዘመድ-ወዳጆቻቸዉን ካጡት አንዱ መንግሥትን ያመሰግናሉ።ወጣትዋም «ሐሪፍ» ነዉ ትላለች-እንደ አነጋገር ፈሊጧ።
የሃያ ዓመትዋ ወጣት ግን ተቃራኒዉን ነዉ የምትለዉ።«ለነብስ ያደሩ» ከሚቸሯት በስተቀር የሚሰጣት ርዳታ የለም።
ወጣትዋ ወላጆችዋን አጥታለች።ሁለት ታናናሾችዋን ታሳድጋለች።ዘላቂነት በሌለዉ ርጥባን።መቶዎች ያለቁበት አደጋ የደረሰበት ምክንያትን እስካሁን ያጣራ የለም።ካለም ተጠያቂዎችን ለሕዝብ አላሳወቀም።የቁሻሻ መከመሪያዉ ሥፍራ ወደ ምርጥ መናፈሻነት እንደሚቀየር የሐገሪቱ ትላልቅ ሹማምንት ተናግረዉ ነበር።አንድ የቁሻሻ ጣይ ድርጅት ባለቤት እንደነገሩን አደጋዉ ከደረሰበት ጀርባ አሁንም ቁሻሻ እየተከመረ ነዉ።
ነጋሽ መሐመድ
ኂሩት መለሰ