የቡራዩ እና አካባቢው ተፈናቃዮች ቅሬታ
ማክሰኞ፣ መስከረም 8 2011ከቡራዩ ተፈናቅለው በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ በሚገኙ የተለያዩ ትምህርት ቤቶች የተጠለሉ ወገኖች ከስምንት ሺህ በላይ ደርሰዋል። ለእነዚህ ተፈናቃዮች የአዲስ አበባ ህዝብ በወጣቶች አስተባባሪነት የዕለት ደራሽ ምግብ እና የልብስ እርዳታ እያደረገ ይገኛል። በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ፣ ወረዳ 18፣ ፊሊጶስ ትምህርት ቤት የተጠለሉ ወገኖች ከመንግስት በቂ እርዳታ አለማግኘታቸው አሳዝኗቸዋል። ከጥቃቱ ያልታደገቸው መንግስት አሁንም በእርዳታ አቅርቦት ዳተኛ መሆኑ “እኛ ዜጎች አይደለንም ወይ?” የሚል ጥያቄ እንዲያነሱ እንዳስገደዳቸው ይናገራሉ።
በቦታው ሲያስተባብሩ የነበሩ የክፍለ ከተማው የሰራተኛ እና ማህበራዊ ጉዳይ ጽህፈት ቤት ኃላፊ መንግስት አስፈላጊውbን ድጋፍ እያደረገ ነው ብለዋል። ተፈናቃዩቹ ግን እስካሁን ከመንግስት ያገኙት አንድ ሺህ ፍራሽ ብቻ እንደሆነ ያስረዳሉ። አብዛኞቹ ተፈናቃዮች ምሽቱን የሚያሳልፉት በተማሪዎች ዴስክ ታጥፈው እንዲሁም ካርቶን አንጥፈው እየተኙ እንደሆነ ይገልጻሉ። ለተፈናቃዩቹ የመመገቢያ ዕቃዎች፣ የውስጥ ልብሶች፣ ለህጻናት ዳይፐር እና ውሃ እንደሚያስፈልጋቸው በቦታው ያሉ አስተባባሪዎች ተናግረዋል። የሚበሉበት ሳህን ስለሌለ ህዝብ የሚያመጣላቸውን ምግብ በፌስታል እየተቋጠረ ሲሰጣቸው የDW ዘጋቢም ተመልክቷል።
ሙሉ ዘገባውን ለማድመጥ የድምጽ ማዕቀፉን ይጫኑ
ዩሃንስ ገብረእግዚያብሔር
ተስፋለም ወልደየስ
ነጋሽ መሐመድ