የቡድን ሐያ-ጉባኤና የገንዘብ ቀዉስ
ረቡዕ፣ ሰኔ 13 2004
ሎስ ካቦስ-ሜክሲኮ ዉስጥ ተሰብስበዉ የነበሩት የቡድን ሐያ አባል ሐገራት መሪዎች የዓለምን በተለይም የአዉሮጳን የገንዘብ ኪሳራ ለማቃለል በጋራ እንደሚጥሩ አስታወቁ።በኢንዱስትሪ የበለፀጉትንና በመበልፀግ ላይ የሚገኙትን ሐገራት የሚያስተናብረዉ ቡድን የመሪዎች ጉባኤ አዉሮጶች የገጠማቸዉን ኪሳራ ለማቃለል የሚያደርጉትን ጥረት አድንቋል።መሪዎቹ በጉባኤያቸዉ ማብቂያ ባወጡት የጋራ መግለጫ እንዳመለከቱት ኪሳራዉን ለማቃለል ከ450 ቢሊዮን ዶላር በላይ ለማሰባሰብ አቅደዋል።የዶቸ ቬለዋ ክሪስቲና በርገርማን የዘገበችዉን የበርሊኑ ወኪላችን ይልማ ሐይለ ሚካኤል እንደሚከተለዉ አጠናቅሮታል።
ሎስ ካቦስ ሜክሲኮ የተካሄደው የቡድን 20 ሃገራት ጉባኤ የዓለም የፋይናንስ ገበያ ተጠናክሮ እንዲያገግም በጋራ ለመሥራት ቃል ገባ ። ትናንት ጉባኤው ሲጠናቀቅ በወጣው መግለጫ እንደተጠቆመው መሪዎቹ ችግሩን ለመፍታት የተቀናጀ የፊናንስ አሰራርን መከተል የሚያስችሉ እርምጃዎች ሥራ ላይ መዋላቸውን እንደሚደግፉ አስታውቀዋል ። በዩሮ ቀውስና መፍትሄው በላይ ቀረቡ ሃሳቦች ላይ የተነጋገረው ይኽው ጉባኤ የዩሮ ተጠቃሚ ሃገራት ዩሮን ለማረጋጋት አስፈላጊ የሆኑትን እርምጃዎች በሙሉ እንደሚወስዱም በመግለጫው ጠቅሷል ። በጉባኤው ላይ የተገኙት የጀርመን መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል በሰጡት አስተያየት አውሮፓ ችግሩን ለመፍታት ከአሁኑ ይበልጥ መተባበር ይገባዋል ብለዋል ።
«በበኩሌ የተጠናከረ አውሮፓ እንደሚያስፈልገን ፣ትብብራችን ይበልጥ ጥብቅ መሆን እንደሚገባው በድጋሚ ግልፅ አድርጌያለሁ ። ምክንያቱም ገበያው የሚፈልገው በአንድ ላይ ወደ ቀድሞው ቦታችን እንድንመለስ ነው ። በተጨማሪም በአውሮፓ ቁጥጥሩና አመኔታው አብሮ የሚሄድና ሚዛኑን ጠብቆ መከናወን የሚገባው መሆኑንም ግልፅ አድርጌያለሁ ። »
የቡድን ሃያ ጉባኤ ተሳታፊታዎች ተጨማሪ የንግድ ማነቆዎችን ቢያንስ ለአንድ ዓመት ያህል ለማዘግየትም ተስማምተዋል ። ለ 2 ቀናት በተካሄደው በዚህ ጉባኤ ማጠቃለያ ላይ የወጣው መግለጫ ይህንኑ በመጨረሻ ደቂቃ ላይ የተደረሰበትን ስምምነት አካቷል ። በዚሁ መሠረት ሃገራቱ እጎአ እስከ 2014 ሃገራቱ ተጨማሪ የንግድ ማነቆ እርምጃዎችን ከመውሰድ ይቆጠባሉ ። ብራዚል አርጀንቲናና ደቡብ አፍሪቃ የንግድ ማነቆው ገደብ የሚያበቃበት ጊዜ ቀድሞም እንደተቀመጠው በ 2013 ያብቃ ባይ ነበሩ ። የተቀሩት ሃገራት ደግሞ እስከ 2015 እንዲራዘም ጠይቀው ነበር ። ይሁንና ለሁለት የተከፈለው ጉባኤ በ ሩስያው ፕሬዝዳንት ቫላድሚር ፑቲን ገላጋይ ሃሳብ መስማማቱን ሮይተርስ ዘግቧል ።
ይልማ ሐይለ ሚካኤል
ነጋሽ መሐመድ
አርያም ተክሌ