የባቡር አደጋ በኢትዮጵያ
ዓርብ፣ መጋቢት 27 2011ማስታወቂያ
ከሰበታ ወደ ጅቡቲ በመጓዝ ላይ የነበረ የኢትዮ-ጅቡቲ ምድርባቡር ኩባንያ ዕቃ ጫኝ ባቡር በደረሰበት አደጋ፤ፉርጎ ጎታች ማሽኑና 17 ፉርጎዎች መበላሸታቸዉ ተነገረ። ባቡሩ አደጋ ያጋጠመዉ ከአዲስ አበባ 129 ኪሎ ሜትር ርቀት ሲደርስ የሚሽከረከርበት ሐዲድ በደለል በመሸፈኑ ሐዲዱን ስቶ ነዉ የሚል ዘገባ ተሰራጭቶ ነበር። ስማቸዉ እንዲጠቀስ ያልፈለጉ አንድ የምድር ባቡሩ ባለሙያ እንደሚሉት ግን አደጋዉ የደረሰዉ ሆን ተብሎ በተሰራ «ሻጥር» ነዉ። ባለሙያዉ እንደሚሉት ምድር ባቡሩን የሚመሩት ሰዎች ሙያዊም ሆነ አስተዳደራዊ ብቃት የሌላቸዉ ናቸዉ። ባቡሮቹን የሚያሽከረክሩትም የቻይና ዜጎች እንጂ ኢትዮጵያዉያን አይደሉም። ትናንት ለዛሬ አጥቢያ የተገለበጠው ባቡር ይጎትታቸዉ ከነበሩ ክፉኛ የተጎዱት ሰወስት ፉርጎዎች ቻይና ካልተላኩ በስተቀር ኢትዮጵያ ዉስጥ መጠገን አይቻልም። ሌሎቹ ፉርጎዎች ግን ጉዳታቸዉ መጠነኛ በመሆኑ አገልግሎት መስጠት እንደሚችሉ ባሉሙያዉ ለዶቸ ቬለ (ዲ ዳብሊዉ) በስልክ ነግረዉናል። የደረሰዉ ጉዳት ወደ 600 ሚሊዮን ብር ይገመታል ተብሎአል። የኩባንያዉ የሕዝብ ግንኙነት ባለሥልጣን ስለ አደጋዉ መግለጫ እንዲሰጡን ብንጠይቅ ለዛሬ አይደርስም ብለዉናል።
ነጋሽ መሐመድ
ኂሩት መለሰ