የብር ምንዛሪ ዋጋ ቀነሰ
ማክሰኞ፣ መስከረም 30 2010ማስታወቂያ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የሐገሪቱን የብር የምንዛሪ ዋጋ በአስራ-አምስት ከመቶ ቀነሰ። ሮይተርስ ዜና አገልግሎት የባንኩን ምክትል ገዢ ጠቅሶ እንደዘገበዉ የምንዛሪዉ ዋጋ የቀነሰዉ የወጪ ንግድን ለማበረታት ነዉ። የኢትዮጵያ ፕሬዝደንት ሙላቱ ተሾመ ትናንት ለሐገሪቱ ምክር ቤት ባደረጉት ንግግር የዉጪ ንግድን ለማበረታት የብር የምንዛሪ ዋጋ እንደሚቀንስ አስታዉቀዉ ነበር። በአዲሱ ተመን መሠረት አንድ የአሜሪካን ዶላር ወደ 27 የኢትዮጵያ ብር ገደማ ይመነዘራል።የገንዘብ አስተዳደር ባለሙያ አቶ አብዱልመናን መሐመድ እንዳሉት የምንዛሪዉ መቀነስ ወደ ሐገር በሚገቡ ሸቆጦች ላይ የዋጋ ንረት ያስከትላል፤ለዉጪ ንግድም የሚኖረዉ አስተዋፅኦ ላጭር ጊዜ ነዉ።ብሔራዊ ባንክ እስካሁን አምስት በመቶ የነበረዉን የወለድ መጠንም ወደ ሰባት ከመቶ ከፍ አድርጎታል። ኢትዮጵያ ከሰባት ዓመት በፊት የብር የምንዛሪ አቅምን በ17 ከመቶ ቀንሳ ነበር።
ነጋሽ መሐመድ
ሸዋዬ ለገሰ