1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

የታላቁ ኅዳሴ ግድብ ምረቃ

ዓለምነው መኮንን
ረቡዕ፣ ጳጉሜን 5 2017

ከ14 ዓመታት በፊት መጋቢት 24 ቀን 2003 ዓ.ም. መሠረቱ የተጣለው ታላቁ የኢትዮጵያ ኅዳሴ ግድብ ዛሬ ጳጉሜ 4 ቀን 2017 ተጠናቅቆ በይፋ ተመርቋል። ምሁራንና ባለሙያዎች የግድቡ ፍፃሜ መድረስ ሌሎች ግዙፍ ፕሮጅርክቶችን መገንባት እንደምንችል ማሳያ ነው እያሉ ነው።

Äthiopien Benishangul-Gumuz-Region | Grand Ethiopian Renaissance Dam
ምስል፦ Office of the Prime Minister-Ethiopia

የታላቁ ኅዳሴ ግድብ ምረቃ

This browser does not support the audio element.

 

«በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት በርካታ ፕሮጀክቶች ይገነባሉ» ጠ/ሚ/ር አቢይ አህመድ

ታላቁ የኢትዮጵያ ኅዳሴ ግድብ ከፍተኛ የዲፕሎማሲ ጫናዎችን ተሻግሮ በኢትዮጵያውያን የገንዘብ መዋጮና ድጋፍ ተገንብቶ ዛሬ ለምረቃ በቅቷል። 233 ቢሊዮን ብር እንደወጣበት የሚነገረው ኅዳሴ ግድብ ዛሬ ሲመረቅ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አቢይ አህመድ እንዳሉት በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት የኒውክሌር ማብላ ያ ተቋምና የነዳጅ ማጣሪያን ጨምሮ የግዙፍ ፕሮጀክቶች ምረቃና ግንባታዎች ይከናወናሉ። በቀጣይ የሚገነቡ ፕሮጀክቶች ከ30 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር በላይ ሀብት እንደሚጠይቁም አመልክተዋል።

የዛሬውን የኅዳሴ ግድብ መጠናቅቀ በማስመልከት አስተያየታቸውን ያካፈሉን አንዳንድ የአማራ ክልል ነዋሪዎች «ንድ ከሆንን የማንሠራው ነገር አይኖርም» ብለዋል።

አስተያየታቸውን ከሰጡን መካከል በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፌደራሊዝምና ሰብዓዊ መብት መምህርና ተመራማሪው ዶ/ር ሲሳይ መንግሥቴ አንዱ ናቸው።

«የግድቡ ግንባታ በርካታ ውስብስብ ችግሮችን አልፏል» ዶ/ር ሲሳይ መንግሥቴ ከአአዩ

ዶ/ር ሲሳይ፣ የምረቃ ሂደቱን ከትናንት ምሽት ጀምሮ ሲከታተሉ እንደነበር አስታውሰው «የግድቡ መጠናቀቅ ደስታ ፈጥሮልኛል» ብለዋል። አፍሪካውያን እንደሚችሉ ኢትዮጵያ ምሳሌ መሆኗን አመልከተው፣ ይህም እንደ ዳግማዊ አደዋ የሚቆጠር ድል እንደሆነ አስምረውበታል። ግድቡ ውስብስብ ሂደቶችን አልፎ እዚህ ደርሷል ያሉት ዶ/ር ሲሳይ፣ «ታሪካዊ» ያሏቸው አካላት የግድቡን ሂደት ለማደናቀፍ ብዙ ቢጥሩም እንዳልተሳካላቸው ተናግረዋል።

በደብረ ብርሀን ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኝነት መምህርና የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ ረዳት ፕሮፌሰር ዳምጠው ተሰማ የኅዳሴ ግድብን ማጠናቀቅ መቻላችን፣ በሕብረትና በአንድነት ከተነሳን ሌሎች ግዙፍ ፕሮጀክቶችን የመፈፀም አቅማችን ማሳያ መሆኑን ተናግረዋል።

የግድቡ መጠናቅቀ ኢትዮጵያውያን ሌሎች ተመሳሳይ ፕሮጀክቶችን ለመገንባት እንደሚችሉ ማሳያ ነውም ብለዋል። በጋራ መሥራት የማይቻል የሚመስለውን እንደሚቻል ኢትዮጵያውያን ለዓለም ማኅበረሰብ አሳይተዋልም ነው ያሉት። 

ምስል፦ AP Photo/picture alliance

«የግድቡ ፍፃሜ ከአደዋ ድል አያንስም» ሰለሞን እሸቱ ከመቅደላ አምባ ዩኒቨርሲቲ

የአደዋና የካራማራ ድሎች ተዋግተን ድል ማድረጋችን የአንድነታችን ምስጢር ነው ያሉት በመቅደላ አምባ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግኑኝነት መምህር ሰለሞን እሸቱ የኅዳሴ ግድብ ፍፃሜም ከዚህ የተለየ እንዳልሆነ አስረድተዋል።

በአማራ ክልል ምሥራቅ ጎጃም ዞን የእነማይ ወረዳ የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊ አቶ ደጉ አያሌው የቦንድ ግዥና የማስተባባር ሥራ ሲሰሩ እንደነበር አስታውሰው ግድቡ ለፍፃሜ መድረሱ እንዳስደሰታቸው ገልጠዋል። መላው የወረዳው ሕዝብ በግድቡ መጠናቀቅና ፍፃሜ በእጅጉ መደሰቱን ነው ለዶይቼ ቬሌ በስልክ የተናገሩት።

ምሁራኑ አሁን በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ያሉ ግጭቶችና ጦርነቶች እንዲወገዱና ሁሉም ለልማት በአንድ እንዲሰለፍ በአዲሱ ዓመት መንግሥትም ሆኑ ነፍጥ አንስተው የሚዋጉ ኃይሎች ወደ ሰላም እንዲመጡም ጠይቀዋል።

በታላቁ የኢትዮጵያ ኅዳሴ ግድብ ምረቃ ከተገኙ የሀገር መሪዎች መካከል የደቡብ ሱዳን፣ የሶማሊያ፣ የኬንያ የጅቡቲና የሌሎችም አገሮች ከፍተኛ ባለሥልጣናት ተገኝተዋል።

ታላቁ የኢትዮጵያ ኅዳሴ ግድብ 1.78 ኬ ሜ ርዝመትና 145 ሜትር ከፍታ ያለው ሲሆን 74 ትሪሊዮን ሊትር ውኃ ይይዛል፣ ግድቡ 5,100 ሜጋ ዋት ኤሌክትሪክ ኃይል የማመንጨት አቅምም እንዳለው ይገለፃል።

ዓለምነው መኮንን 

ሸዋዬ ለገሠ

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ቀጣዩን ክፍል እለፈው የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል እለፈው ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW