1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የታኅሣሥ 8 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ሰኞ፣ ታኅሣሥ 8 2016

በሻምፒዮንስ ሊግ 16ቱ ቡድኖች ድልድል ስዊዘርላንድ ኒዮን ውስጥ ዛሬ ይፋ ሆኗል። አራት ቡድኖችን በማሳተፍ ስፔን ቀዳሚ ሆናለች ። በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ ማንቸስተር ዩናይትድ የሊቨርፑልን ግስጋሴ ሲገታ፤ አርሰናል በአንድ ነጥብ ልዩነት የመሪነቱን ስፍራ ዳግም ተረክቧል። ኢትዮጵያውያቱ አትሌቶች በዓለም መድረክ ገነው የወጡበት ምክንያቱ ምን ይሆን?

Schweiz Nyon 2023 | UEFA Champions League | Trophäe bei Achtelfinal-Auslosung
ምስል Salvatore Di Nolfi/KEYSTONE/dpa/picture alliance

ሣምንታዊ የስፖርት ዘገባ

This browser does not support the audio element.

በሻምፒዮንስ ሊግ የጥሎ ማለፍ ፉክክር ስፔን አራት ቡድኖችን፤ ጀርመን እና ጣሊያን ሦስት ሦስት ቡድኖችን አሰልፈዋል ። እንግሊዝ ሁለት ቡድኖች ለጥሎ ማለፉ ሲያልፉላት፤ ቀሪዎቹ ፈረንሣይ፣ ኔዘርላንድ፣ ፖርቹጋል እና ዴንማርክ አንድ አንድ ቡድን አላቸው ። በጀርመን ቡንደስሊጋ ባለፈው ሳምንት ጉድ የሆነው ባየርን ሙይንሽን ሲጠበቅ በነበረው የትናንቱ ግጥሚያ በአስተማማኝ መልኩ አሸንፏል ። በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ ማንቸስተር ዩናይትድ የሊቨርፑልን ግስጋሴ ሲገታ፤ አርሰናል በአንድ ነጥብ ልዩነት የመሪነቱን ስፍራ ዳግም ተረክቧል።  ማንቸስተር ሲቲ በቅርብ ርቀት ከዋንጫ ፉክክሩ አልወጣሁም ብሏል ። ኢትዮጵያውያቱ አትሌቶች በዓለም መድረክ ገነው የወጡበት ምክንያቱ ምን ይሆን? ቃለ መጠይቅ ይኖረናል ። 

አትሌቲክስ፦

የጎርጎርጎሪዮሱ 2023 ሊጠናቀቅ ከሁለት ሳምንት በታች ብቻ ይቀረዋል ። በሚገባደደው 2023 ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በተለይ ሴቶች አትሌቶቻችን በዓለም የስፖርት መገናኛ አውታሮች በከፍተኛ ደረጃ ስማቸው ገኖ ሲነሳ ነበር ። ከእነዚህ አትሌቶች መካከል፦ የቤርሊን ማራቶን ላይ ክብረወሰን በመስበር ታሪክ ያስመዘገበችው አትሌት ትእግስት አሰፋ ትገኝበታለች ። ትእግስት የቤርሊን ማራቶንን ከ2 ሰከንዶች ማሻሻሏ ከዐርባ ዓመታት ወዲህ የመጀመሪያው ነው ።

ሌላኛዋ ኢትዮጵያዊት አትሌት ጉዳፍ ጸጋዬ፦ የዓለም አትሌቲክስ ምርጥ አትሌቶችን ለመምረጥ ባደረገው የድምፅ አሰጣጥ ለጥቂት አምስቱ ውስጥ ሳትገባ የቀረች ድንቅ አትሌት ነች ። ጉዳፍ በቡዳፔስት ሐንጋሪ የዓለም አትሌቲክስ ከእጃችን ሊወጣ ከጫፍ ደርሶ የነበረውን የ10,000 ሜትር የወርቅ ሜዳሊያ ታግላ ወደ ኢትዮጵያ አስመልሳለች ። 

ኢትዮጵያውያቱ አትሌቶች ጉዳፍ ጸጋዬ (ከመሀል) ወርቅ፤ በስተግራ ለተሰንበት ግደይ ብር እንዲሁም ከግራ ደግሞ እጅጋየሁ ታየ የነሐስ ሜዳሊያ በቡዳፔስት የዓለም አትሌቲክስ የ10,000 ሜትር ውድድር አሸንፈው። ፎቶ፦ ከማኅደርምስል Antonin Thuillier/AFP

በዚሁ ውድድር አትሌት ለተሰንበት ግደይ በበኩሏ የብር ሜዳሊያ ተሸላሚ ነበረች በትውልድ ኢትዮጵያዊ በዜግነት ሆላንዳዊ የሆነችው እና ብርቱ ተፎካካሪዋ አትሌት ሲፋን ሐሰንን ከወደቀችበት ሄዳ አንስታታለች ። በወቅቱ ላደረገችው መልካም ምግባርም ለሽልማት በቅታለች ።  በዓለም መድረክ ለድል ከመብቃትም ባሻገር የስፖርታዊ ጨዋነት ሽልማት አሸናፊ በመሆን የዓለማችን ድንቅ አትሌት መሆኗን አስመስክራለች ። በሚገባደደው 2023 አትሌቶቻችን በዓለም መድረክ ተሳትፎ እና እንቅስቃሴያቸው ምን ይመስል ነበር? በኢትዮ ኤፍ ኤም 107.8 የኢትዮ ኤፍ ኤም ስፖርት ዋና አዘጋጅ እና አቅራቢ ምሥጋናው ታደሰ ።

 የታኅሣስ 1 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

የሻምፒዮንስ ሊግ የጥሎ ማለፍ ድልድል

በሻምፒዮንስ ሊግ በደርሶ መልስ ጥሎ ማለፍ የሚወዳደሩት 16ቱ ቡድኖች ድልድል ስዊዘርላንድ ኒዮን ውስጥ ዛሬ ይፋ ሆኗል ። ወደ ጥሎ ማለፉ ከተሻገሩ 16 ቡድኖች መካከል አራት ቡድኖችን በማሳተፍ ስፔን ቀዳሚ ሆናለች ። ባርሴሎና ከጣሊያኑ ናፖሊ፤ አትሌቲኮ ማድሪድ ከጣሊያኑ ኢንተር ሚላን፤ ሪያል ማድሪድ ከጀርመኑ ላይፕትሲሽ እንዲሁም ሪያል ሶሲዬዳድ ከፈረንሳዩ ፓሪ ሳንጃርሞ ጋ ለማጋጠም ስፔን አራት ቡድኖችን አሰልፋለች ።

ጀርመን ሦስት ቡድኖች ይዛ ትከተላለች ። ከጀርመን ቡድኖች መካከል ላይፕትሲሽ በእጣ ድልድሉ ከባዱ የሪያል ማድሪድ ቡድን ደርሶታል ። በምድባቸው አንደኛ ሆነው ያጠናቀቁት ቦሩስያ ዶርትሙንድ እና ባየርን ሙይንሽን በእጣው በአንጻሩ የተሻለ ቡድን ደርሷቸዋል ።   ባለፈው ሳምንት ከፓሪ ሳንጃርሞ ጋ አንድ እኩል ተለያይቶ የምድቡ መሪ ሆኖ ያለፈው ቦሩስያ ዶርትሙንድ በጥሎ ማለፉ የኔዘርላንዱ ፒኤስቪ አይንድሆቨን ደርሶታል ። ባዬርን ሙይንሽን የጣሊያኑ ላትሲዮን ይገጥማል ። 

ከምስጋናው ጋ የተደረገው ሙሉ ቃለ መጠይቅ እዚህ ይገኛል

This browser does not support the audio element.

የእንግሊዞቹ አርሰናል እና ማንቸስተር ሲቲ ከፖርቹጋሉ ፖርቶ እና፤ ከዴንማርኩ ኮፐንሀገን ጋር ይፋለማሉ ።  የመጀመሪያው ዙር የጥሎ ማለፍ ውድድሮች ማክሰኞ የካቲት 5፣ 6 እንዲሁም በሳምንቱ 12 እና 13 ይከናወናሉ ። ሁለተኛ የመልስ ግጥሚያዎች ማክሰኞ የካቲት 26 እና በነጋታው 27 እንዲሁም በሳምንቱ መጋቢት 3 እና 4 ይከናወናሉ ።  የአውሮጳ ሊግ እጣ ድልድልም ዛሬ ይፋ ሆኗል ። 

እግር ኳስ

ባለፈው ሳምንት «የባየርን ሙይንሽንን አምድ ነቀነቀው» በሚል በጀርመን የስፖርት ጋዜጦች አድናቆት የተቸረው አይንትራኅት ፍራንክፉርት ትናንት በባዬር ሌቨርኩሰን የ3 ለ0 ሽንፈት በተራው ተነቅንቋል ። በአንጻሩ ባዬርን ሙይንሽን ሽቱትጋርትን 3 ለ0 ድል አድርጎ የሽንፈት ሞራሉን አድሷል ። ይኼም ትናንት ነበር በአሊያንትስ አሬና ስታዲየም ። በባዬር ሌቨርኩሰን በ39 ነጥብ ደረጃውን ይመራል ። ባየርን ሙይንሽን በ35 ይከተላል ። 32 ነጥብ ይዞ በቡንደስሊጋው ሦስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ላይፕትሲሽ ቅዳሜ ዕለት ሆፈንሀይምን 3 ለ1 ድል አድርጓል ። ሽቱትጋርት በ31 ነጥብ የአራተኛ ደረጃ ላይ ሲገኝ፤ ቦሩሲያ ዶርትሙንድ 26 ነጥብ ሰብስቦ አምስተኛ ነው ። ከትናንት በስትያ አውግስቡርግን ገጥሞ አንድ እኩል ተለያይቷል ።  ኮሎኝ በ10፤ ማይንትስ እና ዳርምሽታድት በ9 ነጥብ ከ16ኛ እስከ 18ኛ ደረጃ ላይ ይቃትታሉ ።

የባየር ሙይንሽን እንግሊዛዊ አጥቂ ግብ አዳንነቱ ቀጥሏል ። ሽቱትጋርትን ባሸነፉበት የእሁድ ታኅሣሥ 7ቀን፤ 2016 ዓ.ም ግጥሚያ ሁለት ግቦችን አስቆጥሯል ። ምስል Michaela Rehle/AFP/Getty Images

የኅዳር 24 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

የእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ ዘንድሮ ከጀርመኑ በተለየ የነጥብ ፉክክሩ እጅግ ተቀራራቢ በሆነ መልኩ ቀጥሏል ። በመሪው አርሰናል በአንድ ነጥብ ብቻ ተበልጠው የሚከተሉት ሊቨርፑል እና አስቶን ቪላ 38 ነጥብ ሰብስበዋል ። ማንቸስተር ሲቲ እና ቶትንሀም 34 እና 33 ነጥብ ይዘው አራተኛ እና አምስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ ። 

ፕሬሚየር ሊግ

ሊቨርፑል ትናንት በሜዳው አንፊልድ ማንቸስተር ዩናይትድን በጨዋታ ቢበልጥም ያለምንም ግብ ነጥብ ተጋርቶ ተለያይቷል ። ማንቸስተር ዩናይትድ አብዛኛውን ጊዜ  በመከላከል ላይ አተኩሮ መቆየቱ ከሽንፈት ታድጎታል ። ለአርሰናል ደግሞ የገና ሰሞን እፎይታ ሰጥቶታል ። ሊቨርፑል ትናንት ቢያሸንፍ ኖሮ ደረጃውን በ40 ነጥብ መሪ ሆኖ ይቆጣጠር ነበር ። አርሰናል ትናንት ብርቱ ተፎካካሪ የነበረው ብራይተንን 2 ለ0 አሸንፏል ። የማንቸስተር ዩናይትድ፣ እንዲሁም አስቶን ቪላ 2 ለ 1 ብሬንትፎርድን ባሸነፈበት ጨዋታ ከሦስቱም ቡድኖች ሦስት ተጨዋቾች በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብተዋል ።  ዌስትሀም ዩናይትድ ዎልቨርሀምፕተንን፤ ኒውካስል ፉልሀምን 3 ለ0 አሸንፈዋል ።

ሊቨርፑል ትናንት በሜዳው አንፊልድ ማንቸስተር ዩናይትድን በጨዋታ ቢበልጥም ያለምንም ግብ ነጥብ ተጋርቶ ተለያይቷል ። አጥቂው ሉዊስ ዲያዝም ሆኑ ሌሎቹ ቡድኑን ነጥብ ከመጣል አልታደጉም ምስል Rui Vieira/AP/dpa/picture alliance

የፉልሀም አንድ ተጨዋችም የቀይ ካርድ ሰለባ ሆኗል ። ኤቨርተን በርንሌይን፤ ቸልሲ ሼፊልድ ዩናይትድን፤ እንዲሁም አንድ ተጨዋቹ በቀይ ካርድ የተሰናበተበት ቶትንሀም ኖቲንግሀም ፎረስትን 2 ለ0 ማሸነፍ ችለዋል ። የሉቶን ታወን እና የበርመስ ጨዋታ 65ኛ ደቂቃ ላይ አንድ እኩል ሳሉ ተቋርጧል ።  የሉቶን ታወን አምበል   ቶኒ ሎኪየር የልብ ምቱ በመቋረጡ ሜዳው ውስጥ ተዝለፍልፎ መውደቁ በርካቶችን አስደንግጧል ። ተጨዋቹ በዚህ መልኩ ሜዳ ላይ ሲዝለፈለፍ ለሁለተኛ ጊዜ መሆኑም ተዘግቧል ።

ኬንያ የ2024 ን የአፍሪቃ ዋንጫ ከታንዛኒያ እና ከኡጋንዳ ጋ በትብብር እንደምታዘጋጅ ዛሬ ይፋ ሆኗል ። በአፍሪቃ እግር ኳስ ዋንጫ ቀደምቷ ኢትዮጵያ በስታዲየም የጥራት መስፈርት ጉድለት ተጨዋቾቿ ከሀገር ሀገር ለግጥሚያ ይንከራተታሉ ። በመጪው ጥቅምት ወር በሚካሄደው ግጥሚያ አፍሪቃ ውስጥ ያሉ ተጨዋቾችን ብቻ በማሰለፍ 16 ሃገራት ይሳተፉበታል ። 

ማንተጋፍቶት ስለሺ

እሸቴ በቀለ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ከ DW