የታክስ ንቅናቄ በአዲስ አበባ
ረቡዕ፣ ጥር 22 2011ታህሳስ 12 ይፋ የሆነው ሃገር አቀፍ የታክስ ንቅናቄ በአዲስ አበባ ዛሬ ተጀምሯል፡፡ በዘርፉ በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚስተዋሉት የሙስና ፡ የኮንትሮባንድ ፡ ህግን የማስከበር አቅም እና ሌሎች መሰል ችግሮች በአዲስ አበባም እንደሚታዩ ዛሬ አዲስ አበባ ውስጥ በተካሄደ ስብሰባ ላይ ተወስቷል፡፡ ነጋዴዎች ባተረፉት መጠን ፍትሃዊ ገቢ እንዲከፍሉ በፍቃደኝነት ላይ የተመሰረተ የግብር ገቢ ስርዓት ለመዘርጋት እየተሰራ እንደሆነም ተገልጿል፡፡ በአዲስ አበባ ባለፉት 9 ወራት 18.7 ቢሊዮን ብር ገቢ የተሰበሰበ መሆኑ የተጠቀሰ ሲሆን ይሁንና የታክስ ስወራና ህገወጥ ተጠቃሚነት ቢቀረፉ ገቢው ከዚህ በከፍተኛ መጠን ይልቅ እንደነበር የከተማዋ ምክትል ከንቲባ ኢንጂኒየር ታከለ ኡማ ተናግረዋል፡፡ የከተማዋ መስተዳድር ከ 2003 አ/ም ወዲህ ጉዳያቸው ሲታይ የነበሩ 6 ሽህ ነጋዴዎች የተጣለባቸውን ግብር ባለመቀበል አቤት በማለት ሲንገላቱ መቆየቸውን ታሳቢ በማድረግ የግብር ይግባኛቸው ታይቶ የተጫነባቸው እዳ እንዲሰረዝ አደርጓል ብለዋል፡፡ በተጨማሪም ጉዳያቸው በህግ ተይዞ የነበሩ 1780 ነጋዴዎች እዳቸው እንዲሰረዝ ጫፍ ላይ መደረሱንም ይፋ አድርገዋል፡፡ በአጠቃላይ ለታሰበው አላማ መሳካትም በተለይ ግብር ከፋዩ ህብረተሰብ ቀና ትብብር እንዲያደርግ ተጠይቋል፡፡ ሰሎሞን ሙጩ ከአዲስ አበባ ተጨማሪ ዘገባ አለው ።
ሰሎሞን ሙጬ
ኂሩት መለሰ
አዜብ ታደሰ