የትንሳኤ በዓል ዝግጅት በአማራ ክልል
ቅዳሜ፣ ሚያዝያ 26 2016በተለያዩ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና የፀጥታ ችግር ስር በሚገኘው የአማራ ክልል የትንሳኤ በዓልን በተለያዩ ስሜቶች ሆነው ለማክበር ነዋሪዎች መዘጋጀታቸውን ነዋሪዎች ተናገሩ፡፡ ነዋሪዎቹ በአንዳንድ አካባቢዎች ያለው የፀጥታ ችግር የበዓል ግብኣቶች ወደ ገበያ እንዳይደርሱ ማድረጉን ሲገልፁ፣ ሌሎች ደግሞ የግብዓትች ዋጋ በከፍተኛ ደረጃ መጨመሩን ይናገራሉ።
በአንዳንድ አካባቢዎች ግን ብዙም የተጋነነ የዋጋ ጭማሪ እንደሌለ ተገልጧል።
አስተያየታቸውን ለዶይቼ ቬሌ የሰጡ የምዕራብ ጎጃም ደንበጫ ከተማ ነዋሪ የእርድ እንስሳት አቅርቦትም ሆነ ዋጋ ከዘመን መለወጫ ሲነፃፀር የተሻለ ነው፡፡
በዚሁ ዞን የፈረስ ቤት ከተማ አስተዳደር አስተያየት ሰጪ በአንፃሩ በፀጥታ ችግር ምክንት መንገዶች እንደልብ ባለመከፈታቸው የእርድ እንስሳት ወደ ገበያ መግባት እንዳልቻሉ ይናገራሉ፡፡ በመሆኑም የእርድ እንስሳትን ከገጠር ዘመዶቻቸው በቅብብሎሽ ለማምጣት ጥረት እያደረጉ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
በምስራቅ ጎጃም ዞን የደብረማርቆስ ከተማ ነዋሪ የአቅርቦት ችግር ባይኖርም የእርድ እንስሳት ዋጋ በጣም ከፍተኛ እንደሆነ አመልመክተዋል፡፡ አንድ የእርድ ሰንጋ እስከ 100ሺህ ብር እንደሚጠራና አንድ በግ ከፍተኛው እስከ 17ሺህ ብር ሲጠራ ማየታቸውን ገልጠዋል፡፡
በአላማጣ ከተማ የሚኖሩ አንድ መምህር ለዶይቼ ቬሌ በስልክ እንደነገሩት ሰሞኑን በአካባቢው በነበረው የሰላም መደፍረስ ምክንት ደመወዝ በወቅቱ ባለመከፈሉ በበዓሉ አከባበር ላይ የራሱ አሉታዊ ተጽዕኖ እንደፈጠረበት ነው ያስረዱት፡፡
በአማራ ክልል ደቡብ ወሎ ዞን ተሁለደሬ ወረዳ ከሐይቅ ከተማ በቅርብ እርቀት በሚገኘውና በተለምዶ”ቱርክ” እየተባለ በሚጠራው የመጠለያ ጣቢያ ከሚኖሩ ክርስቲያኖች መካከል አንዷ በሰጡት አስተያየት ሰሞኑን የጣለው ከባድ ዝናብ መኖሪያ ድንኳናቸውን በማፍረሱ በተፈናቃይ መጠለያ ሆኖ በዓሉን ለማክበር እንዳልቻሉ ተናግረዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በአፋር ክልል ነዋሪ የሆነውና በማሕበራዊ ሚዲያው “ዘመን ተሻጋሪ” በሚል የሚታወቀው ወጣት አብዱ መሐመድ በጃራ የተፈናቃዮች መጠለያ ለሚኑሩ ተፈናቃዮች በማህበራዊ ዘመቻ ባሰባሰበው 120ሺህ ብር 2 ሰንጋዎችን ገዝቶ ወደ ቦታው እየላከ እንደሆነ ነግሮናል፡፡
ይህ የተነገራቸው ተፈናቃዮችም ሰንጋዎቹን በጉጉት እየጠበቁ እንደሆነ አንድ ተፈናቃይ ነግረውናል፡፡
ወጣቱ ባለፈው የኢድ አልፈጥር በዓል ለሙስሊም ምዕመናን በተመሳሳይ 3 ሰንጋ፣ 120ሺህ ዋጋ ያለው ዱቄት ማስረከቡን ተፈናቃዮቹ አመልክተዋል፡፡
በባሕር ዳር ያለውን የእንስሳት ገበያ እንደተመለከትነው የተወሰነ የአቅርቦት እጥረት አለ፣ ይህን ተከትሎ የአንዳንድ ምርቶች ዋጋ ከፍ ብሏል፤ አንድ በግ 17 ሺህ ብር ዋጋ ተቆርጦለት የተመለከትን ሲሆን መካከለኛ ሰንጋ እስከ 90 ሺህ ብር ሲጠራ ውሏል፡፡
ዓለምነው መኮንን
ታምራት ዲንሳ