የትግራይ ትውልድ ፓርቲ ወይም 'ውድብ ወለዶ ትግራይ' - አዲሱ ተቃዋሚ ፓርቲ
ሰኞ፣ መስከረም 12 2018
የትግራይ ትውልድ ፓርቲ -' ውድብ ወለዶ ትግራይ' - አዲሱ ተቃዋሚ ፓርቲ በትግራይ
ከህወሓት የወጡ የህወሓት ከፍተኛ መሪዎች ጨምሮ በርካታ የቀድሞ የህወሓት አባላት የመሰረቱት አዲስ ፓርቲ በሳምንቱ መጨረሻ በመቐለ ጠቅላይ ጉባኤ አደረገ። የትግራይ ትውልድ ፓርቲ የተሰኘው ይህ አዲስ ፓርቲ፥ በክልሉ ለአዲሱ ትውልድ የሚሆን ፖለቲካዊ መንገድ እንደሚከተል ገልጿል።
ከህወሓት ክፍፍል በኃላ በቀድሞ የህወሓት አባላት እና አመራሮች የተመሰረተ ሁለተኛ ፓርቲ የሆነው 'ውድብ ወለዶ ትግራይ' የትግራይ ትውልድ ፓርቲ በአብዛኛው የምስረታው አስተባባሪዎች እና አባላቱ በአቶጌታቸው ረዳ ይመራ በነበረው የትግራይ ግዚያዊ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች የነበሩ ናቸው። በሳምንቱ መጨረሻ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ተወካዮች በተገኙበት መስራች ጉባኤውን ያደረገው ውድብ ወለዶ ትግራይ ወይም የትግራይ ትውልድ ፓርቲ፥ 'የአዲሱ የትግራይ ትውልድ' ጥያቄ በሚመልስ ሁኔታ ባለው መንገድ ፖለቲካዊ ትግል ለማድረግ ማቀዱን አስታውቋል።
የቀድሞ የህወሓት አመራሮች
ከፓርቲው መስራቾች መካከል በአቶ ጌታቸው ረዳየፕሬዝደንትነት ግዜ የትግራይ ማእከላዊ ዞን ዋና አስተዳዳሪ የነበሩት አቶ ግዑሽ ግደይ፣ የትግራይ ሰሜን ምዕራብ ዞን አስተዳዳሪ የነበሩት አቶ ተክላይ ፍቃዱ እንዲሁም የትግራይ ምስራቃዊ ዞን አስተዳዳሪ የነበሩት አቶ ሰለሙን ትኩዕ ይገኙበታል።ቅዳሜ መስከረም 10 ቀን 2018 ዓመተምህረት በተጀመረው የፓርቲው ጉባኤ ስለ አዲሱ ፓርቲ የተናገሩት ከመስራቾቹ መካከል አቶ ግዑሽ ግደይ፥ የትውልድ ትግል ለማድረግ ፖርቲያቸው ወደ እንቅስቃሴ መግባቱን አመልክተዋል።
አቶ ግዑሽ "ትግራይ በከፋ ሁኔታ ላይ ትገኛለች። ችግሩን የተረዳው የትግራይ ትውልድ ፓርቲ የትግራይ ችግር በታክቲካዊ ሳይሆን ስትራቴጂካዊ በሆነ መንገድ አስቦ ለመመለስ እና ለመምራት የሚሻ ነው። የትግራይ ትውልድ ፓርቲ ለዚህ ትውልድ፣ ለዚህ ዘመን፣ እየኖርንባት ላለችው ምድረ ቀደምት ትግራይ የሚመጥን የትግል አቅጣጫ፣ ፖለቲካዊ ትንተና እና ስነ ሐሳብ ተከትለን ለመስራት፥ በተለይም ደግሞ የአሁኑ ትውልድ ጥያቄን ለመመለስ በልዩ ሁኔታ ይሰራል" ብለዋል።
አዲስ እና ጠንካራ ፓርቲ
ከዚህ በተጨማሪ ስለፓርቲው መስራቾች እና ዓላማዎች የጠየቅናቸው የትግራይ ትውልድ ፓርቲ ምስረታ አስተባባሪ አቶ ሰለሙን ትኩዕ፥ በትግራይ ጠንካራ ፓርቲ ለመፍጠር እየተንቀሳቀሱ መሆኑ ተናግረዋል። በመስራች ጉባኤው በመቶዎች የሚቆጠሩ ከትግራይ የተለያዩ አካባቢዎች የመጡ የፖርቲው ጉባኤ አባላት እና ከህወሓት ውጪ ሌሎች በክልሉ የሚንቀሳቀሩ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች እንዲሁም የተቋማት ተወካዮች ታድመዋል። ያነጋገርናቸው አቶ ሰለሙን ትኩእ "ፖርቲያችን ከህወሓት የተለየ ፓርቲ ነው። በትግራይ ያለው ችግር እጥንተናል። በነፃነት እንተማመናለን፣ ፀረ ዴሞክራሲ ፓርቲ አይደለም" ብለዋል።
የህወሓት ክፍፍል
በህወሓት መካከል የተፈጠረውን ክፍፍል ተከትሎ በአቶ ጌታቸው ረዳ የሚመሩ አካላት የትግራይ ዴሞክራሲያዊ ስምረት የተሰኘ ፓርቲ መመስረታቸው ገልፀው የነበረ ሲሆን ከወራት በፊት 'በቅርቡ ጉባኤ እናደርጋለን' ብለው የነበረ ቢሆንም፥ እስካሁን የተደረገ ነገር የለም። በተጨማሪም ከህወሓት የተነጠሉ ሌሎች አካላት እና ከትግራይ ሐይሎች የተለዩ ታጣቂዎች ማእከላቸው አፋር ክልል አድርገው የትጥቅ ትግልን መጀመራቸው ሲገልፁ ቆይተዋል።
ሚሊዮን ኃይለሥላሴ
አዜብ ታደሰ
ታምራት ነገራ