የትግራይ ክልል ኃይሎችን ለመሸምገል የተደረገው ጥረት
ረቡዕ፣ ነሐሴ 14 2017
የትግራይ ፖለቲካዊ ከነበረው ወደከፋ ሁኔታ መግባቱን የገለፀበትን መግለጫ ያወጣው በትግራይ በተቃዋሚነት የሚንቀሳቀስው ሳልሳይ ወያነ ትግራይ፥ ለሁለት የተከፈለው ህወሓት ደግሞ ከኤርትራ እና ኢትዮጵያ መንግስታት ጋር በማበር የትግራይ ክልል ችግሮችን እያወሳሰበ ነው ብሏል። የሳልሳይ ወያነ ትግራይ ህዝብ ግንኙነት ሐላፊ አቶ ብርሃነ አፅበሃ፥ ከኤርትራ እና ኢትዮጵያ መሪዎች ጋር ያበሩት የህወሓት ሁለት ቡድን መሪዎች ከትግራይ ክልል ህዝብ ዋነኛ አጀንዳዎች በተቃራኒ እየተንቀሳቀሱ ነው ሲሉ ወቅሰዋል።
በትግራይ ክልል በአሁኑ ወቅት ሰላማዊ የፖለቲካ ትግል የሚቃረን እንዲሁም ዴሞክራሲ የሚያጠፉ የኃይል እርምጃዎች መቀጠላቸው፣ በዜጎች ላይ የሚፈፀሙ ግድያዎች፣ እገታዎች እና ሌሎች ወንጀሎች የተለመዱ ሁነቶች ሆነው እንዳለ ሳልሳይ ወያነ ትግራይ አመልክቷል። ከዚህ በተጨማሪ የትግራይ አስተዳደር ከትግራይ ወጥቶ በሌሎች እየተወሰነ መሆኑ ፓርቲው ጨምሮ ገልጿል።
በሌላ በኩል በትግራይ ህዝብ ዘላቂ ጥቅሞች ዙርያ እንደሚሰራ የሚገልፀው የትግራይ ፐብሊክ ዲፕሎማሲ የተባለ የሲቪል ድርጅቶች፣ የሃይማኖት ተቋማት እንዲሁም ሌሎች በትግራይ የሚሰሩ አካላትን ያካተተው አደረጃጀት ባወጣው መግለጫ እንዳለው፥ በቅርቡ በኢትዮጵያ ፌደራል መንግስት እና የትግራይ አመራሮች መካከል ያለውን ልዩነት በተመለከተ ከኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስቴር አብይ አሕመድ ጋር ተወያይቶ ተስፋ ሰጪ ውጤት ማግኘቱን ይገልፃል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ አብዛኞቹ የትግራይ ኃይሎችወታደራዊ አመራሮች ባለፈው ጥር 15 ቀን ያስተላለፊት ለአንድ የህወሓት ክንፍ ያጋደለ የተባለ ውሳኔ ተከትሎ በመካከላቸው ልዩነት መፈጠሩ፥ ይህ ልዩነት ግጭቶች እየፈጠረ መምጣቱ አሳሳቢ እንዳደረገው ሲገልፅ የነበረ ሲሆን፥ በዚህ ጉዳይም የትግራይ ፐብሊክ ዲፐሎማቲክ እየሰራ መሆኑን አስታውቋል። በትላንትናው ዕለትም የአብዛኞቹ ወታደራዊ መሪዎችን ውሳኔ የተቃወሙት ጀነራል ጉዑሽ ገብረ፣ ጀነራል ከበደ ፍቃዱ፣ ኮነሬል ገብረዮሃንስ አባተ ከትግራይ ግዚያዊ አስተዳደር ፕሬዝደንት እንዲሁም የትግራይ ኃይሎች መሪ ጀነራል ታደሰ ወረደ ጋር እንዲገናኙ አብረው እንዲሰሩ ሁኔታዎች መፈጠራቸውን ገልፀዋል። ይህ ተግባር በትግራይ ግጭት እንዳይቀሰቀስ ለሚሻ፣ ሰላም ለሚፈልግ ትልቅ ብስራት ነው ብሏል የትግራይ ፐብሊክ ዲፕሎማሲ።
ሚሊዮን ኃይለሥlላሴ
ኂሩት መለሰ
ልደት አበበ