የኒደርዛክሰን ምርጫ
ማክሰኞ፣ ጥር 14 2005በኒደርዛክሰን የገጠመው ሽንፈት ለሜርክል በመጪው አጠቃላይ ምርጫ የማስጠንቀቂያ ምልክቶች መሆናቸውን ተንታኞች ያስረዳሉ ።
ባለፈው እሁድ በጀርመኑ የኒደርዛክሰን ፌደራዊ ክፍለ ሃገር ምክር ቤት የተካሄደው ምርጫ ውጤት እዚህ ጀርመን ማነጋገሩ ቀጥሏል ። ግዛቲቱን ላለፉት 10 አመታት ያስተዳደረው የክርስቲያን ዲሞክራት ህብረት ፓርቲ በዚህ ምርጫ መሸነፉ በመጪው መስከረም በሚካሄደው የጀርመን አጠቃላይ ምርጫ ውጤት ላይ ከፍተኛ ተፅእኖ ሊያሳድር ይችላል የሚል ግምት አሳድሯል ። ሰሜን ምዕራብ ጀርመን የሚገኘው የኒደርዛክሰን ፌደራዊ ክፍለ ሃገር ከ16ቱ የጀርመን ፌደራል ክፍለ ግዛቶች በስፋት ሁለተኛው ነው ። በህዝብ ብዛት ደግሞ አራተኛውን ስፍራ ይይዛል ። ዋና ከተማይቱ ሃኖቨር ልዩ ልዩ የቴክኖሎጂ ምርቶች የሚተዋወቁባቸው ዓለም አቀፍ ዓውደ ርዕዮችን እንዲሁም ባህላዊ ና የታሪካዊ ትርኢቶች በማስተናገድ የምትታወቅ ከተማ ናት ። ቮክስቫገንና አውዲን የሚያመርተው ትልቁ የአውቶሞቢል ኢንዱስትሪ ቮክስዋገን ፤ የሚገኝበት በዚሁ ግዛት ሥር ያለው ቮልፍስቡርግ የተባለው ከተማም የንግድና የኢንዱስትሪ ማዕከል ነው ። ሌሎችም የንግድ እንቅስቃሴዎች የሚያመዝንባቸው ከተሞች የሚገኙባትን የኒደርዛክሰን ፌደራዊ ክፍለ ግዛት ወግ አጥባቂው የክርስቲያን ዲሞክራት ህብረት ፓርቲ በጀርመንኛው ምህፃር CDU ና ግራ ዘመሙ የሶሻል ዲሞክራቶች ፓርቲ SPD እየተፈራረቁ መርተዋል ።
SPD ከ1946 እስከ 1955 ከዚያም 1959 እስከ 1976 በኋላም ከ1990 እስከ 2003 ድረስ ፣ CDU ደግሞ እ.ጎ.አ ከ1955 እስከ 1959 እንዲሁም ከ1976 እስከ 1990 ከዚያም ከ2003 እስከ 2013 ድረስ ኒደርዛክሰንን አስተዳድረዋልል ። ባለፈው እሁድ በተካሄደው ምርጫም ግዛቲቱን ለ 10 ተከታታይ አመታት የመራው CDU ባልተጠበቀ ሁኔታ ሲሸነፍ SPD ና አረንጓዴዎቹ በምክርቤት አብላጫ መቀመጫ በማግኘታቸው በግዛቲቱ የበላይነቱን ይዘዋል ። በአሁኑ ምርጫ CDU 14 የምክር ቤት መቀመጫዎን ሲያጣ SPD ደግሞ 1 ተጨማሪ መቀመጫ አሸንፏል ። አረንጓዴዎቹ ደግሞ እስከዛሬ ከፍተኛ የተባለ 14 በመቶ የመራጭ ድምፅ በማሸነፍ ካለፈው ምርጫ በ6 በመቶ ከፍ ያለ ውጤት አስመዝግበዋል ። ወሳኝ የተባለው የዚህ ምርጫው ውጤት መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ለሚመሩት CDU ታላቅ ሽንፈት ከመሆኑም በላይ በመጪው አጠቃላይ ምርጫ ላይም ከፍተኛ ተፅዕኖ እንደሚያሳድር ተገምቷል ። እዚህ ጀርመን ፍራንክፈርት ነዋሪ የሆኑት የፖለቲካ ተንታኝ ዶክተር ለማ ይፍራሸዋ የከትናንት በስተያው የኒደርዛክሰን ምክር ቤት ምርጫ ውጤት እንዲህ ገምግመውታል ።
የኒደርዛክሰኑ ምርጫ ውጤት ለ CDU ማስጠንቀቂያ ተድርጎ ነው የተወሰደው ። ገዥው CDU ባለፉት 2 አመታት ውስጥ በ 5 ፌደራል ክፍለ ግዛቶች በSPD ተሸንፏል ። CDU ከተሸነፈባቸው ግዛቶች ውስጥ ለረዥም ጊዜ ሲያስተዳድር የቆየው ደቡባዊው ባድን ቩርተንበርግና ፣ የብዙ ህዝብ መኖሪያ የሆነው ራድዮ ጣቢያችን የሚገኝበት የኖርድራይን ቬስትፋለን ፌደራል ክፍለ ግዛቶች ይገኙበታል ። በእነዚህና ከትናንት በስተያ በኒደርዛክሰን የገጠመው ሽንፈት ለሜርክል በመጪው አጠቃላይ ምርጫ የማስጠንቀቂያ ምልክቶች መሆናቸውን ተንታኞች ያስረዳሉ ። ከዚህ ሌላ ውጤቱ በሜርክል አገዛዝ ላይ ችግር ሊፈጥር እንደሚችልም ይነገራል ። ዶክተር ለማ ምክንያቱን ያብራራሉ
በሌላ በኩል SPDም ቢሆን በግዛቱ ያገኘው 1 ተጨማሪ መቀመጫ በመሆኑ ያን ያህል የሚያዝናናው እንዳልሆነ ነው ዶክተር ለማ ያስረዱት ። በግዛቲቱ ያለ ጥርጥር አሸናፊዎች አረንጓዴዎች ብቻ መሆናቸው ነው ተደጋግሞ ይነገራል ። ኒደርዛክሰን በ1970ዎቹ የግዛቱቱ መንግሥት ይደግፈው የነበረውን የኒክልየር ዝቃጭ ማስወገጃ ይቃወሙ የነበሩ የጀርመን የአካባቢ ጥበቃ ተሟጋቾች አንዷ የእንቅስቃሴ ማዕከል ነበረች ። ይህንም መሰሉ ተቃውሞም እጎገ በ1980 የአርንጓዴዎቹ ፓርቲ ምስረታ እውን እንዲሆን አድርጓል ።
ሂሩት መለሰ
ሸዋዬ ለገሠ