የኔቶ አባል ሐገራት የሁለት ቀናት ጉባኤ ኔዘርላንድ ዉስጥ ተጀመረ
ማክሰኞ፣ ሰኔ 17 2017
የሰሜን አትላንቲክ ጦር ቃል ኪዳን ድርጅት (ኔቶ) አባል ሐገራት መሪዎች ዛሬ ኔዘርላንድስ ዴንሃግ ላይ የሁለት ቀናት ጉባኤ ጀመሩ።የ32ቱ አባል ሐገራት መሪዎች የጋራ ፀጥታና ደህንነትን ለሚጠብቀዉ ድርጅት ተጨማሪ ገንዘብ ለማዋጣት ይስማማሉ ተብሎ ይጠበቃል።ይሁንና ጉባኤተኞቹ ሊያዋጡ የሚፈልጉት ወይም የሚችሉት የገንዘብ መጠን የድርጅቱ ዋና አባል የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ እንዲጨመር የሚፈልጉትን ያሕል መሆኑ ብዙ አጠራጥሯል።ጉባኤዉ የተደረገዉ የሩሲያና የዩክሬን ጦርነት ፍፃሜ ና የዋሽንግተን የወደፊት ሚና በግልፅ ባልታወቀበት ሁኔታ ነዉ። የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ሁለተኛ የስልጣን ዘመናቸዉን ከጀመሩ ወዲህ በኔቶ ስብሰባ ላይ ሲገኙ የዛሬዉ ለመጀመሪያ ጊዜ ይሆናል።አዲሱ የኔቶ ዋና ፀሀፊ ማርክ ሩት ጉባኤዉን ለመጀመሪያ ጊዜ ይመራሉ። ሩት ጉባኤዉ ከመጀመሩ በፊት በሰጡት መግለጫ አሜሪካ በኢራን ላይ የወሰደችው ጥቃት ዓለም አቀፍ ህግን የጣሰ አይደለም ሲሉ ተናግረዋል።
«በእውነቱ፣ አስፈላጊ በሆኑ ነገሮች ላይ እናተኩር። የእኔ ትልቁ ፍርሃቴ ኢራን የኒውክሌር ጦር መሳሪያ ባለቤት መሆን እና የኑክሌር ጦር መሳርያን መጠቅም ላይ ነዉ። ይህ ለእስራኤል እና ለመላ ቀጣናዉን ብሎም ሌሎች የዓለም ክፍሎች ማነቆ ይሆናል። እና ለዚህ ነው ኔቶ ኢራን የኒኩሌር መሳርያ ባለቤት መሆን የለባትም የሚለዉ ። ይህ የኔቶ ቋሚ አቋም ነው ። ኢራን ኒውክሌር ጦር መሳሪያን በእጇ መያዝ የለባትም። ስለዚህ ዩናይትድ ስቴትስ ያደረገችዉ ነገር ከዓለም አቀፍ ህግ ጋር የሚቃረን ነው ብዬ አልስማማም»