የአለም የምግብ ቀን
ማክሰኞ፣ ጥቅምት 6 2005የFAO ዋና ፀኃፊ ኾዜ ግራዚያኖ ዳ ዚልፋ እንዳሉትም « ከኑሮው ዋጋ መጨመር ገበሬዎቹ ባለፉት አመታት አትራፊ አልነበሩም፣ የምግብ ዋጋም መቀነስ ይኖርበታል።» ። በአለም ዙሪያ ዛሬ 870 ሚልዮን ሰው ፣ማለትም ፣ ከየ8ቱ አንዱ በቂ ምግብና መጠጥ ውሀ አያገኝም። በተለይ ከሰሀራ በስተ ደቡብ ባሉ የአፍሪቃ ሀገራት እና በእስያ፤ ሁኔታው እጅግ አሳሳቢ መሆኑ ተገልጿል።
የአለም የምግብ እና የእርሻ ድርጅት በምህፃሩ FAO ዛሬ የሚታሰበውን የአለም የምግብ ቀን አሰመልክቶ ከዋሽንግተኑ የምግብ ፖሊሲ ምርምር ተቋም ጋ በመተባበር ከጥቂት ቀናት በፊት በአለም የተራበውን ህዝብ ቁጥር ለመገመት የሚያስችል አንድ የአለም የረሃብ መዘርዝር አውጥቶዋል። ይኸው ለ7ኛ ጊዜ የቀረበው መዘርዝር ባልተመጣጠነ አመጋገብ የተጎዱ፣ ክብደታቸው ከእድሜያቸው ጋ ያልተመጣጠነ ከ5 አመት በታች የሆኑ ህፃናት፣ እንዲሁም ዕድሜአቸው አምስት አመት ሳይሞላ የሚሞቱ ህፃናትን ጉዳይ ትኩረት ሰጥቶዋል። በዚሁ አንጻር የገበሬ ማህበራት ድርሻ ትልቅ መሆኑን በአለም የምግብ እና የእርሻ ድርጅት በፆታ እኩልነት እና በገጠሩ አሰራር ክፍል የተሰማሩትን ኖራ ኦራባህዳድ ገልጾዋል።
« የገበሬ ማህበራት የምግብ ዋስትናን በማረጋገጡ ፣ እንዲሁም ፣ ረሀብን በመቀነሱ ረገድ ሚና ይጫወታሉ። ምክንያቱም ለኤኮኖሚ እና ለማህበራዊ ኑሮ ገፅታዎች ትኩረት በመስጠት ለመንቀሳቀስ የሚሞክሩ በአርአያነት ሊጠቀሱ የሚችሉ ናቸውና። »
አብዛኞቹ በረሀብ የተጠቁ ሰዎች የሚኖሩት በደቡብ እስያ እና ከሰሀራ በስተ ደቡብ ባሉ የአፍሪቃ ሀገራት እንደሆነ ጥናቱ አመልክቶዋል። የዛሬው ቀን ለምን መታሰብ እንደሚገባው ሲያብራሩ፤
በወቅቱ የተራበ ህዝብ ቁጥር ትንሽ ባይሆንም ካለፉት አመታት ጋ ሲነፃፀር ቁጥሩ በመቀነስ ላይ ይገኛል ያሉት የምግብ ፖሊሲ ምርምር ተቋም ባልደረባ ጀርመናዊው ክላውስ ፎን ግሬምበር አንዳንድ አገሮችን በምሳሌነት ጠቅሰዋል።
«ከ1990 እስከ 2012 ዓም ። 15 አገሮች የአለም ርሃብ መዘርዝራቸውን በ50 ከመቶ ወይንም ከዚያን በላይ ሊቀንሱ ችለዋል። ትልቅ ለውጥ ካስመዘገቡ አገሮች መካከል አንጎላ ፣ ባንገላደሽ፣ ኢትዮጲያ ፣ ማላዊ ኒካራጉዋይ ፣ ኒጀር እና ቬትናም ትልቅ ውጤት አስመዝግበዋል።»
በአለም የረሃብ መዘርዝር የመጨረሻውን ቦታ ከያዙት አንዷ ሰሜን ኮሪያ ናት። የረሃቡ ሁኔታ በዚች አገር ይበልጥ መስፋፋቱን ግሬምበር ገልጸዋል። ለረሃብ መስፋፋት እንደ ምክንያት ከተጠቀሱት መካከል የመሬት መቀራመት አንዱ ነው። እንደ የ FAO ፕሬዚዳንት ቤርብል ዲክማን በተለይም ይህ የአፍሪቃ ትናንሽ ገበሬዎችን መተዳደሪያ እየጎዳ ይገኛል።
«ቻይና፣ ቪየትናምና የአውሮፓ አገሮችም ጭምር በአለም ዙሪያ መሬት ይገዛሉ። በአሁኑ ጊዜ ስለ መሬት መቀራመት ብቻ ሳይሆን ስለ ውሃ መቀራመትም ለመናገር እንችላለን። እህል ለማምረት ይቻል ዘንድ በውሃ ሀብት የታደሉ አካባቢዎችንም መግዛት ተጀምሮዋል።» ይህ ጎጂ አሰራርን ለማስወገድ ይቻል ዘንድ ዲክማን እንደ መፍትሄ የጠቀሱት ትናንሽ ገበሬዎችን በምርቱ ሂደት በማካተት የትብብር ስራ መፍጠርን እና ገበሬውንም የትርፉ ተቋዳሽ ማድረግን ነው።
ልደት አበበ
አርያም ተክሌ