1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአረብና የሙስሊሙ አለም-እና ፕሬዝዳት ኦባማ

ረቡዕ፣ ጥር 20 2001

ኦባማ እንዳሉት የዩናይትድ ስቴትስ ለሙስሊሙ አለም እድገትና ደሕንነትን ትሻለች።ትደግፋለችም። ቀዳሚያቸዉና ብጤዎቻቸዉ ያደረሱትን ጥፋት «አንዳዴ ስሕተት ይፈጠራል» ብለዉ አለፉትና ---

ኦባማምስል AP / DW

የዩናይትድ ስቴትሱ ፕሬዝዳት ባራክ ኦባማ ሐገራቸዉ ከአረብና ከሙስሊሙ አለም ጋር በመከባበር ላይ የተመሠረተ አዲስ ትብብር ለመጀመር እንደምትሻ አስታወቁ።ኦባማ የፕሬዝዳትነቱን ሥልጣን ከያዙ ወዲሕ ለመጀመሪያ ጊዜ በሰጡት ቃለ-ምልልስ እንዳሉት አሜሪካዉያን የሙስሊም አረቦች ጠላታቶች አይደሉም።ኦባማ በአረብኛ ቋንቋ ከሚያሰራጨዉ ከአል-አረቢያ ቴሌቪዥን ጣቢያ ጋር ባደረጉት በዚሁ ቃለ ምልልስ እስራኤልና ፍልስጤሞች አዲስ የሰላም ድርድር እንዲጀምሩ ጠይቀዋል።መስተዳድራቸዉ ከኢራን ጋር በቀጥታ ለመደራደር መዘጋጀቱንም አስታዉቀዋል።ZORAN ARBUTINA የዘገበዉን ነጋሽ መሐመድ አጠናቅሮታል።

አል-አረቢያ የኦባማን መግለጫ ከማሰራጨት፣ ሌሎች መገናኛ ዘዴዎች እየተቀባበሉ ከማሰራጨት-ማስተንተናቸዉ ቀደም ብሎ በመካከለኛዉ ምሥራቅ አዲሱ የዩናይትድ ስቴትስ ልዩ መልዕክተኛ ጆርጅ ሚቼል አካባቢዉ ደርሰዉ ነበር።ሰኞ።ለዚያ ምድር ሰላም ዩናይትድ ስቴትስ ብዙ የመጣሯን ያክል-ብዙ መጯናን ኦባማ ተቹ።የእሳቸዉ ይለያልም-አሉ።
ድምፅ

«ጆርጅ ሚቼል ከፍተኛ እዉቅና ያላቸዉ ሰዉ ናቸዉ።አለም አቀፍ የሠላም ድርድሮችን በመሸምገል በሳል አለም አቀፍ ልምድ ካላቸዉ ጥቂት ሰዎች አንዱ ናቸዉ።እና እኔ ያልኳቸዉ ከማድመድ ይጀምሩ ነዉ።ምክንያቱም ዩናይትድ ስቴትስ ብዙ ጊዜ መመሪያ መስጠት ነዉ።የጉዳዮቹን አስፈላጊ ገፅታዎች ግን ብዙ አናዉቃቸዉም።ሥለዚሕ እስኪ እንስማ።»

እስራኤል እራስዋን የመከላከል መብት እንዳላት፥ የአሜሪካ ድጋፍ እደማይጓደልባትም ኦባማ በድጋሚ አስረግጠዋል።የዚያኑ ያክል እስራኤልና ፍልስጤሞች፥ እስራኤልና ሌሎች ጎረቤቶችዋ ሰላም እንዲያወርዱ መስተዳድራቸዉ አበክሮ ይጥራል።

«ሁለቱም ወገኖች የሚከተሉት መንገድ ለሕዝቦች ብልፅግናና ደሕንነት እንደማይጠቅም የሚረዱበት ጊዜ አሁን መሆኑን ይቀበሉታል የሚል ተስፋ አለኝ።ይልቅዬ ወቅቱ ወደ ድርድር ጠረጴዛ የሚመለሱበት ነዉ።በርግጥ ከባድ ነዉ።ጊዜም ይጠይቃል።»

ኦባማ እንዳሉት የዩናይትድ ስቴትስ ለሙስሊሙ አለም እድገትና ደሕንነትን ትሻለች።ትደግፋለችም። ቀዳሚያቸዉና ብጤዎቻቸዉ ያደረሱትን ጥፋት «አንዳዴ ስሕተት ይፈጠራል» ብለዉ አለፉትና ዩናይትድ ስቴትስ ከሰላሳ-ከአርባ አመታት በፊት ከሙስሊሙ አለም ጋር የነበራትን መልካም ግኙነት አስታወሱ።ያኔ የተቻለዉ-አሁን የማይቻልበት ምክንያት የለም።ቀጠሉ ፕሬዝዳቱ።
ድምፅ

«ባጠቃላይ ባካባቢዉ ካተኮርን፥ከአረቡና ከሙስሊሙ አለም ጋር ከተገናኘን፥ በመከባበር እና በጋራ ጥቅም ላይ የተመሠረተ ግንኙነት እንዲፈጠር ለማነሳሳት ከተዘጋጀን ትርጉም ያለዉ እመርታ እናሳያለን ብዩ አምናለሁ።»

ኦባማ የኢራንን አወዛጋቢ የኒኩሌር መርሐ ግብር በተመለከተ ከቴሕራኖች ጋር በቀጥታ ለመደራደር ዝግጁ መሆናቸዉን ከምርጫ ዘመቻቸዉ ጊዜ ጀምሮ አስታዉቀዉ ነበር።አሁንም ደገሙት።
ድምፅ

«ከኢራን ጋር ባለን ግንኙነት-ዲፕሎማሲን ጨምሮ ዩናይትድ ስቴትስ ያላትን አቅም በሙሉ መጠቀማችንን ማረጋገጥ በጣም አስፈላጊ ነዉ።በበአለ-ሲመት ንግግሬ እንዳልኩት ኢራንን የመሳሰሉ ሐገራት በጡንቻ መታበያቸዉን ካቆሙ እጃችንን በረጅሙ እንዘረጋላቸዋለን።»

በተባበሩት መንግሥታት የዩናይትድ ስቴትስ አምባሳደር ሱዛን ራይስም መስተዳድራቸዉ ከኢራን መሪዎች ጋር በቀጥታ መደራደር ትሻለች የሚለዉን የኦባማን መርሕ አሰልሰዉታል።ኦቦማ የቀድሞዉ ፕሬዝዳት ጆርጅ ደብሊዉ ቡሽ የከፈተቱት የኹዋንታናሞ መታጎሪያ እንዲዘጋ አዘዋል።ቡሽ ዉቅድቅ ያደረጉትን የከባቢ አየር ጥበቃ መርሕ እንደሚለዉጡት አስታዉቀዋል።አሁን ደግሞ ከቡሽ-የሰይጣን ዛቢያዎች ካንዷ ጋር እንደራደራለን አሉ።

Arbutina,Zoran

Negash Mohammed

Quelle:ZPR

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW