በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሦስት ወረዳዎች የእንስሳት ወረርሽኝ ተቀሰቀሰ
ሰኞ፣ መጋቢት 8 2017
የአንስሳት ወረርሽኝና የመከላከሉ ጥረት በደቡብ ኢትዮጵያ
የእንስሳት በሽታው ከባለፈው ሳምንት አጋማሽ ጀምሮ የተከሰተው በክልሉ ጋሞ ዞን ጋርዳ ማርታ ፣ በደቡብ ኦሞ ዞን ማሌ እና በጎፋ ዞን ኡባ ደብረፀሐይ በተባለ ወረዳዎች ውስጥ ነው ፡፡ በወረዳዎቹ እስከአሁን በሺህዎች የሚቆጠሩ የቤት እንስሳት መሞታቸው እየተነገረ ይገኛል ፡፡ ምንነቱ በውል አልታወቀም በተባለው በዚሁ በሽታ በእርሻ ሥራ ላይ የነበሩ በሬዎቻቸው ጭምር እየሞቱባቸው እንደሚገኙ ለዶቼ ቬለ የተናገሩ አንድ የጋሞ ዞን ጋርዳ ማርታ ወረዳ አርሶአደር “ በሽታው በጣም ከባድ ነው ፡፡ አንዴ ከጀመረ በአፋቸው እና በአፍንጫቸው የማያቋርጥ ፈሳሽ ይወጣል ፡፡ በቆሙበት ወድቀው ነው እየሞቱ ያሉት ፡፡ በተለይ እያረሱ የነበሩ በሬዎች እዛው እርሻ ውስጥ ወድቀው እየሞቱ ነው “ ብለዋል ፡፡
የበሽታው ምንነት
በወረዳዎቹ የእንስሳት ወረርሽኝ መከሰቱን ያረጋገጠው የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ በበኩሉ አሁን ላይ የበሽታውን ምንነት የመለየት ሥራ በመከናወን ላይ እንደሚገኝ አስታውቋል ፡፡ በዝናብ መግቢያ እና መውጫ ወቅቶች ላይ አፈር ወለዱ የሆኑ በሽታዎች የመቀስቀስ ባህሪ እንዳላቸው የጠቀሱት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ሃላፊው ዶክተር አዲሱ እዮብ “ አሁን የበሽታውን አይነት ለመለየት ጥረት እየተደረገ ይገኛል ፡፡ የበሽታው ናሙና በሁለት የእንስሳት ቤተ ሙከራ ተወስዶ ምርመራ እየተደረገበት ይገኛል “ ብለዋል ፡፡
የመከላከል ጥረት
አሁን ላይ በሽታው የተከሰተባቸው ጋሞ ዞን ጋርዳ ማርታ ፣ በደቡብ ኦሞ ዞን ማሌ እና በጎፋ ዞን ኡባ ደብረፀሐይ ወረዳ ወሰን የሚጋሩና እንሰሳቱ ከአንድ ወንዝ የሚጠጡ በመሆናቸውን በሽታው በተመሳሳይ ወቅት መከሰቱን ምክትል ቢሮ ሃላፊው ጠቅሰዋል ፡፡ ዋናው ትኩረታችን እስከአሁን ስንት እንስሳት ሞቶ ሳይሆን ወረርሽኙን እንዴት እንቆጣጠር የሚለው መሆኑን የተናገሩት ምክትል ቢሮ ሃላፊው “ የሽታውን ምንነት ከመለየት ጎን ለጎን በቀጣይ ሊያደርስ የሚችለውን አደጋ ለመቀነስ እየሠራን እንገኛለን ፡፡ በአሁኑወቅት የእንስሳት ህክምና ባለሙያዎች ቡድን ወደ ሥፍራው በማንቀሳቀስ በሥፍራው ደርሰው የመከላከል ሥራ ጀምረዋል “ ብለዋል ፡፡
ሸዋንግዛው ወጋየሁ
ታምራት ዲንሳ
አዜብ ታደሰ