የአውሮጳ ኅብረት ፕሬዚደንት በአፍሪቃ ኅብረት
ሐሙስ፣ የካቲት 19 2012ሊቢያን ጨምሮ በአፍሪቃ የሚታዩ ግጭቶችን ለማስወገድ የአፍሪቃ ሕብረት የሚያደርገዉን ጥረት የአዉሮጳ ሕብረት እንደሚረዳ የአዉሮጳ ሕብረት ኮሚሽን ፕሬዚዳንት ኡርዙላ ፎን ደርላይን ገለፁ።ፎን ደርላይን አዲስ አበባ ላይ ዛሬ በተጀመረዉ 10ኛው የአውሮጳ እና የአፍሪካ ኅብረትቶች የጋራ ስብሰባ ላይ፣ ሕብረታቸዉ ከአፍሪቃ ጋር መቆሙ ለአፍሪቃ አህጉር ልማት በጣም አስፈላጊ ነዉ ሲሉ ተናግረዋል።
«አፍሪቃ በዓለም ፈጣን የኤኮኖሚ እድገት በማስመዝገብ ላይ ያሉ ሃገራት መገኛ ናት።መንግስታትና ህዝቡ ይበልጥ አንድ እየሆኑ ነው። ከአፍሪቃ የሰላም ማስከበር ተልዕኮ አንስቶ እስከ አዲሱ የነጻ ንግድ አካባቢ ድረስ ባሉ ጉዳዮች ላይ ከፍተኛ ፍላጎት አላቸው።እንደ አውሮጳ መጻኤ እድላችሁን በእጃችሁ ማድረግ ትፈልጋላችሁ።ስለዚህ ለወደፊቱ የጋራ ጉዞአችን ልንንነጋገርባቸው የሚገቡ በርካታ የጋራ ነጥቦች አሉ።አፍሪቃ ስትጠናከር እኛም እንጠናከራለን ብዬ ከልብ አምናለሁ።»
የሊቢያን ጦርነትን ለመቅረፍ የአፍሪቃ እና የአዉሮጳ ኅብረት ትብብር አስፈላጊነት እንደምሳሌ የሚጠቀስ ነዉ፤ በሌላ በኩል ሰላማዊ መፍትሄን ገቢራዊ ለማድረግ የሊቢያ ጉዳይ እንደ ጥሩ ምሳሌ የሚጠቀስ ነዉ ሲሉ ፎንደር ላይ ገልፀዋል። አዲስ አበባ ላይ እየተካሄደ በሚገኘዉ 10ኛዉ የአውሮጳ እና የአፍሪካ ኅብረት የጋራ ስብሰባ ላይ ለመገኘት ወደ አዲስ አበባ ካቀኑት ከአዉሮጳ ሕብረት ኮሚሽን ፕሬዚዳንት ኡርዙላ ፎን ድርላይን ጋር 20 የአዉሮጳ ኅብረት ከፍተኛ ባለስልጣናትን ይገኛሉ።
የአውሮጳ ኅብረት ፕሬዚደንት ኡርዙላ ፎን ደር ላይን ከአፍሪቃ ኅብረት ፕሬዚደንት ሙሣ ፋኪ ማኃማት ጋር የሥራ ስብሰባ አድርገዋል። የሁለቱ መሪዎች ንግግርን በማከል የአዲስ አበባው ወኪላችን ጌታቸው ተድላ ኃይለ-ጊዮርጊስ የባለሞያ አስተያየት አክሎ ዘገባ ልኮልናል። አስተያየት ሰጪው ባለሞያ ቀደም ሲል በኅብረቱ አማካሪ የነበሩ እና በአኹኑ ወቅት በግል የማማከር ሥራ ላይ የተሰማሩ የፖለቲካ ተንታኝ ናቸው።
ጌታቸው ተድላ ኃይለ-ጊዮርጊስ
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ነጋሽ መሐመድ