የአውሮጳ የመሪዎች ጉባዔ ዉጤት
ዓርብ፣ ሰኔ 22 2004መሪዎቹ አስራ-ስምንት ጊዜ ተሰብስበዉ ነበር።የመሪዎቹን ጉባኤና ዉሳኔያቸዉን የተከታተሉ ወገኖች እንዳሉት እስካሁን የተደረጉት ጉባኤዎች ኪሳራዉ የሚቃለልበትን የረጅም ጊዜ እቅድ አልነደፈም ነበር።
ትናንት ተጀምሮ የዛሬ የቀጠለዉ ጉባኤ ግን ለከሰሩት መንግሥታት ብድርና ርዳታ መስጠት ብቻ ሳይሆን ባንኮቻቸዉንም በቀጥታ ለመርዳት ወስኗል።አዲሱ ዉሳኔ ግን የጀርመንዋ መራሒተ-መንግሥት ወይዘሮ አንጌላ ሜርክል እንዳሉት የቀድሞዉን መርሕ የሚያጠናክር እንጂ የሚሽር አይደለም።«
በዚሕ ረገድ እስካሁን የተከተልነዉን መርሕ በሙሉ እንደያዝን እንቀጥላለን።ምግባር፥ አፀፋ ምግባር፥ቅድመ-ሁኔታና ቁጥጥር አለ።ይሕን በተመለከተ በጣም ጠቃሚ ነገር ነዉ ያከናወነዉ ብዬ አምናለሁ።ይሁንና ካንዱ ወገን ሲደረግ የሚደረግለትም ወገን ሐላፊነቱን መወጣት አለበት የሚለዉ ፍልስፍናችን አሁንም እንዳለ ነዉ።በዛሬዉ ስምምነት መሠረት ኪሳራን ለመቋቋም ከሚቀመጠዉ ገንዘብ ብድርና ርዳታ የሚያገኙ መንግሥታት ወይም ተቋማት የሚሰጣቸዉን ገንዘብ ባግባቡ ሥራ ላይ ማዋላቸዉን፥ ከኪሳራዉ ለመዉጣት የሚያደርጉትን ጥረትና መዉሰድ ያለባቸዉን እርምጃ በትክክልና በተገቢዉ ጊዜ መዉሳዳቸዉ ይገመገማል።ስምምነቱን የአዉሮጳ ሕብረት ምክር ቤት ፕሬዝዳት ሔርማን ሮምፖይ ታላቅ እመርታ ብለዉታል።«አዲስ ስምምነት አድርገናል።ይሕ ታላቅ እመርታ ነዉ።ምክንያቱም ባንኮች በቀጥታ ወረት ያገኛሉ።ከሁሉም በላይ በጣም ጠቃሚዉ ነገር አንድ ወጥ የመቆጣጠሪያ ሥልት እንዲኖር መወሰናችን ነዉ።ሁለተኛዉ ደግሞ ከኪሳራ ለመዉጣት ጥሩ ምልክት የሚያሳዩ ሐገራትን ለማበረታትና ገበያዉን ለማረጋጋት አባል መንግሥቶቻችን የገንዘብ ማረጋጊያ ተቋማት ማለትም የEFSF እና ESM ድጋፍ እንዲያገኙ መወሰናችን ነዉ።»
ነጋሽ መሐመድ
ተክሌ የኋላ