1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአውሮፓ ህብረት የስደተኞች አቀባበል መርህ

ዓርብ፣ ነሐሴ 3 2005

በትንሽቷ የአውሮፓ ህብረት አባል ሃገር ማልታ የባህር ጠረፍ በሰዎች የተጨናነቁ ጀልባዎች ማረፊያ አጥተው ሁሌም ይጉላሉ ። በተደጋጋሚ በሜዲትራኒያን ባህር ላይ ጀልባዎች ይገለበጣሉ ፤ ይሰጥማሉ ሰዎችም ይሞታሉ ። ይሁንና በየቀኑ የአፍሪቃና የእስያ ስደተኞች ራሳቸውን ለአደጋ አጋልጠው በጀልባዎች ወደ ማልታ መምጣታቸው አልቆመም ።

ምስል picture alliance/dpa

ሳብሪና ፓብስት እeደዘገበችው በሺህዎች የሚቆጠሩ ስደተኞች ማልታን ወደ መሳሰሉ ሃገራት የሚመጡት ከርስ በርስ ጦርነት ፣ ከድህነትና ከጭቆና በመሸሽና የተሻለ ህይወት ፍለጋም ነው ። ይሁንና ማልታን በመሳሰሉ የአውሮፓ ህብረት ድንበር ሃገራት ለብዙ ችግሮች ይጋለጣሉ ።
የተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽን በምህፃሩ UNHCR እንዳስታወቀው ባለፉት 6 ወራት ማልታና ኢጣልያ የባህር ጠረፎች የገቡት ስደተኞች ቁጥር 8400 ነው ። 415 ሺህ ነዋሪዎች ብቻ ላሏት ማልታ የስደተኞቹ ቁጥር እጅግ ከፍተኛ ነው ። የህብረቱ ድንበር የሆኑት ማልታን የመሳሰሉ ሃገራት በስደተኞች እየተጥለቀለቁ ነው ።

በሜዴትራንያን ባህር ልትስጠም የነበረች ስደተኞች የጫነች ጀልባምስል picture-alliance/dpa

እነዚህ ስደተኞችም በማልታ ለተለያዩ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ይጋለጣሉ ። ፕሮ አዝዩል የተባለው በአውሮፓ ተገን ማግኘት ለሚፈልጉ ስደተኞች መብት የሚቆመው ድርጅት ቃል አቀባይ ካርል ኮፕ ስደተኞቹ ማልታን ወደ መሳሰሉ ሃገራት በብዛት ቢጎርፉም መንግሥታት የሰብዓዊ መብታቸው መጣስ እንደሌለበት ያሳስባሉ ። « የአውሮፓ ህብረት ድንበር የሆኑት ሃገራት በከፊል በስደተኞች ተጨናንቀዋል ። ሆኖም ሃገራቱ በስደተኞች መጨናነቃቸው በምንም ዓይነት በነዚህ ሃገሮች ከፍተኛ የሰብዓዊ መብት ክፉኛ እንዲጣስ ሰበብ ሊሆን አይገባም ። »ግሪክም ስደተኞች በብዛት ከሚጎርፉባቸው አገሮች አንዷ ናት ። ህገ ወጥ የሚባሉ ስደተኞች ወደ ግሪክ የሚመጡት በባህር ብቻ ሳይሆን በቱርክ በኩል በየብስም ጭምር ነው ። እንደ ማልታ ሁሉ የግሪክ የስደተኞች መጠለያዎችም ተጨናንቀዋል ። የአውሮፓ ድንበር ወደ ሆኑት ሃገራት የሚመጡ ስደተኖች ከወዲህ ወዲያ እንደሚለጋ ኳስ ከሃገር ሃገር እንዲከራተቱ ይደረጋል ። ለምሳሌ በመጀመሪያ ኢጣልያ የደረሱ ስደተኞች እዚያ የተገን ማመልከቻ አስገብተው ወደ ሌላ

አፍሪቃውያን ስደተኞች በኢጣልያምስል AP

የአውሮፓ ህብረት አባል ሃገር ቢሄዱ መጀመሪያ ወዳመለከቱበት ሃገር መልሰው ይልኳቸዋል ። ስደተኞቹ እንደምንም ብለው ጀርመን ኔዘርላንድ ወይም ስዊድን ቢገቡ ተመልሰው ወደ ሜዴትራኒያን ባህር አዋሳኝ ሀገሮች የመባረር እጣ ሊገጥማቸው ይችላል ። ጀርመን በአሁኑ ጊዜ በግሪክ በኩል የመጡ ስደተኞችን መልሳ ወደ መጡበት አትልክም ። የጋራው የአውሮፓ የስደተኞች አቀባበልና አያያዝ መርህ ከሰኔ መጀመሪያ አንስቶ ተግባራዊ ሆኗል ።የአውሮፓ ህብረት ከዚያ በፊት በነበረው አቋም የስደተኞች ጉዳይ በተናጠል መታየት ያለበት ጉዳይ አድርጎ ነበር የሚወስደው ። ተገን ጠያቂዎችን የሚመለከተው ፖለቲካ አሁን በመላው አውሮፓ በህግ እልባት ሊደረግለት ይገባል ይላሉ አክስል ፎስ በአውሮፓ ፓርላማ የወግ አጥባቂው የCDU ተወካይ

ስደተኖች በለምፔዱዛምስል picture-alliance/dpa

« አሁን ያለው ሁኔታ የእያንዳዱ ሃገር በተናጠል ሳይሆን በጋራ የሚወጣው ጉዳይ ነው ።
በአረቡ ዓለም ህዝባዊ ንቅናቄ በአንድ ጊዜ ብዙ ስደተኞች ወደ አውሮፓ ህብረት መምጣታቸው በግልፅ ታይቷል ። በዚህም አባል ሃገራትን ስደተኞችን ተቀብሎ በማስተናገድ ረገድ ከአቅም በላይ ሆኖ ታይቷል ። »

ስለዚህ ፎስ የጋራ የሆነ መፍትሄ መገኘት አለበት ሲሉ ሃሳብ ያቀርባሉ ። ይህም ሲባል ታዲያ ሰዎች በተለይ በጦርነት ሳቢያ ከትውልድ ሃገራቸው የሚፈናቀሉትን ሆኖም ጦርነቱ ካለቀ በኋላ መመለስ የሚሹትን ነው ። ካርል ኮፕ ግን ህብረቱ የተሳሳተ ቀውስ የማስወገጃ መንገድ እየተከተለ ነው ሲሉ ነቅፈዋል ።
« ብዙ ሰዎችን ከማፈስና አዳዲስ ማጎሪያ ጣቢያዎችን በአውሮፓውያን ገንዘብ ከመገንባት ይልቅ ሰብዓዊ ክብርን በሚጠብቅ መልኩ ግሪክ ውስጥ መጠለያ ጣቢያዎችን በገንዘብ መደገፍ በተቻለ ነበር ። ከዚህም ጋር ተያይዞ ህዝቦቻቸውን አፍነው የሚይዙ መንግሥታትን ማስወገድ በተቻለ ነበር ። »

ሂሩት መለሰ

ሸዋዬ ለገሰ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW