የአይሲስ ቡድን በሊቢያ?
ረቡዕ፣ ኅዳር 17 2007ዴርና የምትባለው የሊቢያ ባህር ዳርቻ ላይ የምትገኘው ከተማ 100 ሺ ያህል ነዋሪ አላት። ከዚች ከተማ እስከ የወደብ ከተማዋ ቤንጋዚ 270 ኪ ሜ ይርቃል። ዴርና ውስጥ 800 የሚጠጉ ሰዎች ናቸው ሶርያ እና ኢራቅ ውስጥ የሚንቀሳቀሰውን እና ራሱን« እስላማዊ መንግሥት ሲል የሚጠራውን ቡድን እንደተቀላቀሉ የተሰማው። ቡድኑ በባህር ዳርቻው ሀገር መሰረት መጣሉ ብዙም የሚያስደንቅ አይደለም ይላሉ አብደል ጋዋድ፤ ጋዋድ ካይሮ የሚገኝ የአሜሪካ ዮንቨርስቲ የፖለቲካ መምህር ፕሮፌሰር ናቸው። « አይሲስ ሊቢያ ውስጥ ያለውን ምስቅልቅል በመጠቀም የነባር የሙስሊም ቡድናት አባላትን ታማኝነት እና ታዛዥነት ለማግኘት እየጣረ ይመስለኛል። አንዳንድ የሙስሊም ቡድናት ባለፉት ጊዜያት ጥገኛ ሳይሆኑ በራሳቸው ይመሩ ነበር ሌሎች ደግሞ የአልቃይዳ ቡድን መረብ አካላት ነበሩ። እዚህ ሊቢያን ጨምሮ የሚታየው ታማኝነትን የመቀየር እንጂ አዲስ ኃይል እና በርካታ ተዋጊዎችን ለአይሲስ የመመልመል ሁኔታ አይለደም ድርና ውስጥ ያለው።»
ከሁለት ሳምንት ገደማ በፊት የአይ ኤስ ቡድን ባሰራጨው የድምፅ መልዕክት ራሳቸውን መሪ አድርገው የሰየሙና አቡ ባኪር አል ባግዳዲ ነኝ የሚሉት ሰው ድምፅ የአይ ኤስ ቡድንን አመለካከት የሚራመዱት በሶርያ እና ኢራቅ ብቻ እንዳልሆነ ይተነትናል። « ሙስሊሞች ሆይ። አይዟችሁ። እኛም በአዲስ ዜና እናስደስታችኋለን። « እስላማዊው መንግሥት» ከ ሳውዲ አረቢያ፣ እስከ የመን፣ ግብፅ ፣ሊቢያ እና አልጄሪያ ድረስ እየተስፋፋ መጥቷል። በዚህም አጋጣሚ በነዚህ ሀገራት አይሲስን እንደምንከተል እንገልጿለን። እና የዚህም ቡድን የሀገር ውስጥ መጠሪያ የእስላማዊው መንግስታት እንለዋለን። እናም ተከታዮቻችንን እናሰማራለን።»
የአይሲስ መሪ አል ባግዳዲ ዴርና ተወልደው ያደጉትን አቡ ናቢል አል አንባሪ የሚባሉ ሰው በሊቢያ የቡድኑ ተጠሪ እንዲሆኑ ሾሞዋቸዋል። ኢራቃዊው አል ባግዳዲ ከሊብያዊው ጋር የተዋወቁት ኢራቅ በነበረው የዩ ኤስ አሜሪካ የምርከኞች ጣቢያ እንደሆነ ይናገራሉ። እንደ አል ባግዳዲ፤ ዴርና የሚሆነው ሁሉ በአል አንባሪ ቁጥጥር ስር ነው። በዚህም መሠረት ቡድኑ ከፍተኛ ስራ ማስፈጸሚያዎችን፣ ፍርድ ቤቶችን፣ ሕፃናት ማሳደጊያዎችን እና አንድ የራዲዮ ጣቢያን በቁጥጥሩ አውሏል። ይህንንም የሚያስፈፁሙ የአይ ኤስ ተፋላሚዎች በስፍራው ይገኛሉ ነው የሚባለው።
የአይሲስ ቡድን ጥቁር ባንዲራውን በዴርና ካውለበለበ በኋላ ፖለቲከኞች ፣ ጠበቆች እና የጦር ጣቢያዎች በአይሲስ ቡድን ኢላማ ውስጥ እንደገቡ ተገልጿል። ቡድኑ በስፍራው የሚገኝ አንድ የእግር ኳስ ስፓዲዮም ውስጥ አንገት ቆርጦ ግድያ የፈፀመበትንም ቪዲዮ ታይቷል። የፖለቲካው ፕሮፌሰር ጋዋድ የአይሲስ ቡድን ልክ እንደ ሶርያ እና ኢራቅ በቀላሉ ሊቢያ ውስጥ ቡድኑን የሚቀላቀሉ ሰዎችን ያሳምናል ብለው አያምኑም። እንደዚያም ሆኖ ምዕራባውያን ሊቢያ ውስጥ የሚሆነውን በቸልተኝነት ሊመለከቱት አይገባም ባይ ናቸው።« ይሄ በቀስታ የሚራመደው የአሜሪካውያንም ሆነ የአውሮፓውያን ፖሊሲ ለአይሲስ መንገድ የሚከፍት አጋጣሚ ፈጥሯል። ምናልባትም እድል አለመስጠት ይቻል ነበር። ይህንን ምሳሌ ወደ ሊቢያ ልናመጣው እንችላለን። ያ ማለት አስቀድሞ መዘጋጀት እና ማሰብ ያስፈልጋል። እንደሚመስለኝ መደረግ ያለበት ትክክለኛው ውሳኔ ይሄ ነው። በመካከለኛው ያለው ሁኔታ እጅግ ወሳኝ ነው። ርምጃ ካልተወሰደ ቀጣይ ወጪው በጣም ከፍተኛ ነው የሚሆነው።
ፔተር ሽቴፈ / ልደት አበበ
ነጋሽ መሀመድ