ከ3600 በላይ ባብዛኛው የቀበሌ ቤቶች መፍረሳቸው ተናግሯል
የአዲስ አበባ እምብርት ፒያሳ፦ መንግሥት ከተማዪቱን ለማዘመን ባለው ርምጃ ፈርሳለች ። በእቴጌ ጣይቱ አስተውሎት እና በዳግማዊ አጤ ምንሊክ ፈቃድ አዲስ አበባ በ1879 የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ሆና ተቆረቆረች ። የከተማዪቱ ቀዳሚ ዘመናዊ አካሏ የነበረችው ፒያሳ ዘንድሮ ከአንድ ክፍለ ዘመን በኋላ በትዝታ ማኅደር ውስጥ ብቻ በነበር ቀርታለች ።
ጠቅላይ ሚንስተር አብይ አሕመድ የከተማዪቱን ባለስልጣናት በዚህ ሳምንት ማክሰኞ ሰብስበው እንዳነጋገሩ ዐስታውቀዋል ። «የአዲስ አበባ የኮሪደር ልማት ሥራ ሂደት» ያሉትን በገመገሙበት ስብሰባም ባለስልጣናቱ በፈረሳው እንዲገፉበት ትእዛዝ አስተላልፈዋል ።
የፒያሳ ፈረሳ በጠቅላይ ሚንስትሩ እና ባለስልጣናቱ አንደበት፦ «አዲስ አበባን አፍርሶ የመሥራት፥ መልሶ መገንባት» ድርጊት ነው ተብሏል ። ድርጊቱም «የማጽዳት» በሚል በባለስልጣናቱ በተዋረድ በተደጋጋሚ ተገልጧል ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ እና ባለስልጣናቱ ፈረሳውን የሚያከናውኑት «አዲስ አበባን እንደ ስሟ አዲስ» ማድረግ መሆኑን በተደጋጋሚ ተናግረዋል ።
ብዙዎች ስለ ፒያሳ አራት ኪሎና የአዲስ አበባ የጥንት መንደሮች ፈረሳ ሲናገሩ፦ ዋነኛ ዐላማው «ልማት» ሳይሆን ሌላ መሆኑን ያብራራሉ ። የከተማዪቱን ኅብረተሰብ የቆየ ጠንካራ ትስስር የመበጣጠስ፥ ታሪክ እና ቅርስ የማውደም አካል ነውም ሲሉ አስረግጠው ይናገራሉ ።
ፒያሳ የተሟላ የከተማ ሕይወት መሠረት፣ መገለጫም ነበረች። ትያትር ቤቶች፣ ሙዚቃ ቤቶች ፣ የትዳር ቀለበት ፣ ሰዓት፣ መነጽር ፣ አልባሳት ቤቶች፣ በጥቅሉ የዘመናዊነት ምልክቶች ሁሉ ፒያሳ ውስጥ ነበሩ። አሁን ግን ፈርሳለች።
ምስል Solomon Muchie/DWከራስ መኮንን ድልድይ ወደ ሲኒማ አምፒየር ወርቅ ቤቶች የነበሩበት ስፍራ
በዚህ ስፍራ ውስጥ ታሪካዊ ኬክ ቤቶች ፣ ወርቅ ቤቶች፣ ልብስ መሸጫ ቤቶች ፣ ቡና ቤቶች ይገኙበት ነበር
ምስል Solomon Muchie/DWየአሁኑ የሀገር ፍቅር ትያትር ስያሜው ሀገር ፍቅር ማሕበር በሚል ነበር በ 1927 ዓ.ም የተመሰረተው። ማሕበሩ የተመሠረተበት ዋናው ዓላማም ፋሺስት ጣልያን ኢትዮጵያን ለመውረር መዘጋጀቱን ተከትሎ የኢትዮጵያን ሕዝብ ለማንቃትና በአንድነት እንዲቆም ለማድረግ የተቋቋመ ነው። የሀገሪቱ አንቱ የተባሉ የኪነ ጥበብ ሰዎችም ታላላቅ ሥራዎችን የሠሩበት ነው።
ምስል Solomon Muchie/DWከራስ መኮንን ድልድይ አለፍ ብሎ የነበረ ግዙፍ ሕንፃ
የራስ መኮንን ድልድይ ለመጀመርያ ጊዜ በ 1903 በዐፄ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት በኖራ ግንብ የተሠራ ነው። ድልድዩን አለፍ ብሎ በታችኛው መስመር የሚገኘው ይህ ግዙፍ ሕንፃ ልዩ ልዩ ሱቆች የሚገኙበት ነበር ።
ምስል Solomon Muchie/DWአራት ኪሎ የአርበኞች ሃውልት ፊህ ለፊት የነበረ ሕንፃ
የአራዳ እምብርት ከሆኑት ሥፍራዎች አንዱ የአራት ኮሎው የአርበኞ አደባባይ ሲሆን ዙሪያውን በትምህርት ሚኒስቴር፣ በጆሊ ባር የተከበበ ሲሆን ይህ ሕንፃ በአንደኛው አቅጣጫ የሚገኝ ነበር)
ምስል Solomon Muchie/DWየሀገር ፍቅር ትያትር ከፋሽስት ጣልያን ወረራ በኋላ በ1933 የኢትዮጵያ ሕዝብ የሀገር ፍቅር ማሕበር ተብሎ በተንጣለለው ግቢ ቢዘልቅም ቅጥር ግቢው ሕጋዊ ካርታ ያገኘው ነሐሴ 9 ቀን፣ 2010 ዓ.ም ነበር። በቅርቡም እድሳት ተደርጎለታል። ሕዝብን በኪነ ጥበብ ለማነሳሳት የተቋቃመው ይህ የአሁኑ ትያትር ቤት የጥበብ ቤት ሆኖ የሀገሪቱን እንቁ የኪነጥበብ ባለሙያዎች አፍርቷል።
ምስል Solomon Muchie/DWመኮንን ባቅላቫ ቤት በአዲስ አበባ ከተማ ለብዙ ባለትዳሮችና ፍቅረኞሞች የታሪካቸው አካል ነበር። ፒያሳ ላይ ለ63 ዓመታት የሠራው ይህ ቤት ከ1953 ዓም ጀምሮ እስከ 2016 ዓ .ም ብዙዎችን አገልግሏል። ዛሬ ታሪክ ሆኗል።
ምስል Solomon Muchie/DWጣይቱ ሆቴል አካባቢ የሚገኝ እድሜ ጠገብ ሆቴል
ጣይቱ ሆቴል በኢትዮጵያ የመጀመርያው ዘመናዊ ሆቴል ነው። አሁን በእድሳት ላይ ይገኛል። ከዚህ ሆቴል አጠገብ ብዙ ሆቴሎች፣ ምግብ ቤቴች እና ቡና ቤቶች ይገኛሉ። ከእነዚህ መካከል ይህ አንዱ ነበር።
ምስል Solomon Muchie/DWከአያሌው ሙዚቃ ቤት ፣ ወደ ዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ አደባባይ
ድምፃዊ የግጥምና ዜማ ደራሲ እንዲሁም የሙዚቃ አቀናባሪ ነው፤ አንጋፋዉ አርቲስት አያሌዉ መስፍን። ወሎ የሙዚቃ ባለ ሙያዎችን የሙዚቃ ምሁራንን፤ ያፈራች መሆንዋን አብዛኞች ይመሰክሩላታል። «አያሌዉ መስፍን ሙዚቃ ቤት ጋር እንገናኝ» የብዙ ሰዎች የቀጠሮ ቃል ነበር።
ምስል Solomon Muchie/DW ጠቅላይ ሚንስትር አብይ «ቅርስ ማለት ምን ማለት ነው?» ሲሉ ጠይቀው ራሳቸው መልስ ሰጥተዋል ። «ማንም ያቦካው ጭቃ ሁሉ ቅርስ አይደለም» ሲሉም አጣጥለው ተናግረዋል ። ቅርስ ምን እንደሆነም ለባለስልጣናቶቻቸው አብራርተዋል ። በእርግጥ ቅርስ ማለት ምንድን ነው? ብዙ የአዲስ አበባ ትውስታዎች እና ታሪካዊ ቤቶችን ያቀፈችው አራዳ ወይንም ፒያሳን እንዲህ በጥድፊያ ማፍረስ ያስፈለገው ለምንድን ነው? የከተማዪቱ ነዋሪ ኅብረተሰብስ ተጎጂ ሳይሆን ተጠቃሚ እንዲሆን ምን ያህል ተሳታፊ ተደርጓል?
በሳምንታዊው የአንወያይ መሰናዶ ካተኮርንባቸው ዐበይት ጉዳዮች የተወሰኑት ናቸው ። በውይይቱም 3 እንግዶች ተሳትፈዋል ።
1- ሠይፈ-ሥላሴ አያሌው (ዶ/ር)፦ የእናት ፓርቲ ፕሬዚደንት እና የትብብር ፓርቲዎች የወቅቱ ሊቀመንበር እንዲሁም
2- ወ/ሮ እናት ዓለም መለሠ፦ የአዲስ አበባ ኮሙኒኬሽ ኃላፊ
3- አቶ ክንፈ-ሚካኤል ኃይለ-ሥላሴ፦ በጀርመን ሀገር የሥነ-ሕንጻ ባለሞያ
ሙሉ ውይይቱን በድምፅ ማጫወቻው ማድመጥ ይቻላል ።
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ነጋሽ መሐመድ