1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአገው ብሔራዊ ሸንጎ ተቃዉሞ

ሐሙስ፣ ታኅሣሥ 25 2016

አዲስ አበባ ውስጥ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ጽ/ቤት ጋዜጠኞችን ጠርቶ ይፋዊ መግለጫ የሰጠው የአገው ብሔራዊ ሸንጎ የፖለቲካ ድርጅት የአገው ህዝብ እራስን በራስ የማስተዳደር ህገመንግስታዊ መብቱን ሳይሸራረፍ እንዲጎናጸፍ አልሞ እንደሚታገል አስታውቋል፡፡

የአገው ብሔራዊ ሸንጎ አመራሮች
የአገው ህዝብ እራስን በራስ የማስተዳደር መብ ገቢራዊ አልተደረገም ሲሉ የአገው ብሔራዊ ሸንጎ አመራሮች ከሰዋልምስል Seyoum Getu/DW

የአገው ብሔራዊ ሸንጎ ተቃዉሞ

This browser does not support the audio element.

የአማራ ክልላዊ  መንግስትና በዋግ ሕምራ ብሔራሰብ አስተዳደር ሸምቆ ሲዋጋ የነበረዉ ስንቀሳቀስ የነበረው የአገው ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (አዴን) በቅርቡ ያደረጉትን የሰላም ስምምነት የአገው ብሔራዊ ሸንጎ አጣጥሎ ነቀፈዉ።የአገው ብሔራዊ  ሸንጎ መሪዎች ዛሬ አዲስ አበባ ውስጥ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳሉት ድርድሩ ሁሉንም የአገው ፖለቲካ ድርጅቶችን ማሳተፍ ነበረበት። ፓርቲው በተለያዩ አከባቢዎች በአማራ ክልል በአገው ብሔረሰብ ተወላጆች ላይ ይፈጸማሉ ያላቸው አድሎ እንዲቆምም ጠይቋል።

ዛሬ ረፋዱን አዲስ አበባ ውስጥ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ጽ/ቤት ጋዜጠኞችን ጠርቶ ይፋዊ መግለጫ የሰጠው የአገው ብሔራዊ ሸንጎ የፖለቲካ ድርጅት የአገው ህዝብ እራስን በራስ የማስተዳደር ህገመንግስታዊ መብቱን ሳይሸራረፍ እንዲጎናጸም አልሞ እንደሚታገል አስታውቋል፡፡

ከአማራ ክልል የሰላም ሥምምነት የተፈራረመው የአገው ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ አመራሮች ሹመት እንደሚሰጣቸው ሊቀ-መንበሩ ተናገሩ

ፓርቲው በመግለጫው በርካታ ወጣቶች ባሁን ወቅት የፓርቲውን ዓላማ አንግበው እስከ ህይወት መስዋዕትነት እየከፈሉ ይገኛሉ ስልም ነው የገለጸው፡፡ ሰላማዊ የፖለቲካ ትግልን አማራጭ አድርጎ እንደምንቀሳቀስ ያሳወቀው ፓርቲው፤ ሆኖም እንደ ፖለቲካ ድርጅት ይፈጸምብኛል ያለው እስራት፣ ከመኖሪያ ቤት የማፈናቀል እና የንብረት ዘረፋ ያሏቸው እንግልቶች ህዝብ መሃል ሆኖ ትግሉን መምራት አዳጋች አድርጎብኛልም ብሏል፡፡ ፓርቲው በዛሬው መግለጫው በአገው ሸንጎ ፓርቲ ስም ህዝብም እየተጠቃ ነው በማለት ከሷል፡፡ ፓርቲው ለመግለጫው በጽሁፍ ያዘጋጀውን ይዘት ለመገናኛ ብዙሃን ያነበቡት የአገው ብሔራዊ ሸንጎ ምክትል ሊቀመንበር ፍታለው አባይ ናቸው፡፡

የአገዉ ብሔራዊ ሸንጎ ፓርቲ ፕሬዝደንት መግለጫ ሲሰጡምስል Seyoum Getu/DW

በዚህም አማራ ክልል ውስጥ መንግስት ለዓመታት በክልሉ ለሚገኙ ብሔሮች በተለይም ለአገው ህዝብ እራስን በራስ የማስተዳደር መብ ገቢራዊ ያልተደረገ ነው ሲል ተችቷል፡፡ የልዩ ዞኖቹን ምክር ቤቶችንም “የይስሙላ” ያለው ፓርቲው ምክር ቤቶቹ አመራሮቻቸውን በቀትታ የመምረጥ ስልጣናቸውን እንኳ በአግባቡ የማይወጡ በማለት ከሷል፡፡ ፓርቲው በመግለጫው በቅርቡ በዋግ ኽምራ ልዩ አገው ዞንና በአዊ የብሔረሰብ ዞን በህዝቡ ከፍተኛ ቅቡልነት አላቸው ያሏቸው ኃላፊዎች ያለ አግባብ ከኃላፊነታቸው ተነስተዋል በማለት የክልሉን መስተዳድር ወቅሷል፡፡

2013 ዓ.ም. ውስጥ እራሱን የአገው ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (አዴን) ብሎ “በትጥቅ የአገው ብሔረሰብ መብትን ለማስጠበቅ” ጫካ መግባቱ ብነገርም ከሰሞኑ የቡድኑ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ከአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ጋር በተግባቦት አጠናቀቀ የተባለውንም ድርድር ፓርቲው ነቅፎ አጣጥሎታል፡፡ “ድርድሩ የግለሰቦች ፍላጎት የተንጸባረቀበት እንጂ የአገው ህዝብ ፖለቲካዊ ፍላጎትን ከግብ የሚያደርስ አይደለም” በሚልም ነው የወቀሰው፡፡

ታጣቂዎች እጃቸውን ሰጡ እየተባለም በአማራ ክልል የቀጠለው ውጊያ

ስለሆነም የአገው ብሔራዊ ሸንጎ የአገው ህዝብ ወቅታዊ ተግዳሮቶችን በጥልቀት በመገምገም የአቋም መግለጫ ማውጣቱን አስረድተዋል፡፡ ከሰሞኑ በአማራ ክልል እና አዴን መካከል የተደረሰው ስምምነት በጫና የተደረገ በመሆኑ ሁሉም የአገው የፖለቲካ ድርጅቶችን ያሳተፈ ድርድር እንዲደረግ ሲል ጠይቋል፡፡ የብሔረሰብ ምክር ቤቶች ስልጣን ተጥሶ ያለ ብሔረሰቡ ይሁኝታ አመራርን ከመሾም የክልሉ  መንግስት ይቆጠብ ሲልም ጠይቋል፡፡ የክልሉን መንግስት በሰራ ክሰውም መንግስት የህዝብን ደህንነት የማስጠበቅ ኃላፊነቱን እንዲወጣ ሲል ነው ሸንጎው የጠየቀው፡፡

የአገው ብሔራዊ ሸንጎ አመራሮች በአማራ ክልል ታስረው ይገኛሉ ያሏቸው 500 የሚሆኑ የብሔረሰቡ አባላት ከእስር እንዲለቀቁ ጠይቀዋል።ምስል Seyoum Getu/DW

የአገው ብሔራዊ ሸንጎ በአቋም መግለጫው አክሎም በክልሉ ደርሷል ያለው ግድያ፣ መፈናቀልና የተለያዩ ወንጀሎች በገለልተኛ አካላት ተጠንቶ ህዝቡ እንዲካስ ሲል ነው የጠየቀው፡፡ የአገው የማንነትና የራስ አስተዳደር ይከበርልኝ ጥያቄ በማቅረባቸው በአማራ ክልል ታስረው ይገኛሉ ያሏቸው 500 የሚሆኑ የብሔረሰቡ አባላት ከእስር እንዲለቀቁ ሲል ጠይቋልም፡፡ “ከስራቸው የተፈናቀሉ 600 የቅማንት ሰራተኞች ወደ ስራ ገበታቸው እንዲመለሱና በደህንነት ስጋት ወደ ሱዳን የተሰደዱ 10 ሺኅ ገደማዎች ወደ ቀዬያቸው እንዲመለሱና ከተቀናጀ እገታ እንዲጠበቁ” ሲል ፓርቲው ጠይቋልም፡፡

 በአማራ ክልል ሁለት ዞኖች ከ85 ሺህ በላይ እንስሳት ከድርቅ ጋር በተያያዘ መሞታቸውን ባለሥልጣናት ገለጹ

ዋግሕምራ ላስታ አገው ላይ በከፋ ሁኔታ ደርሷን ያለው የድርቅ አደጋ ተገቢው ትኩረት እንዲያገኝ በማለትም ፓርቲው ጠይቋል፡፡ የፌዴራል  መንግስትም ለብሔረሰቡ ተገቢ ያለውን ጥበቃ እንዲያደርግ፤ በአማራ ክልል የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ድርጅቶችም በሰጥቶ መቀበል መርህ ለህዝቦች እፎታ መስራት በሚስችል ሰላማዊ መንገድ ላይ አብሮ ለመስራት እንዲቻል ሲል ጥሪ አሰምቷል፡፡

የአገው ብሔራዊ ሸንጎ ከአገው ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (አዴን) ጋር ያለው ፖለቲካዊ ግንኙነት አለው ወይ በሚል ከጋዜጠኞች ለተነሳም ጥያቄ ምላሽ የሰጡት የፓርቲው ሊቀመንበር አቶ ዓላምረው ይርዳው ፓርቲያቸው በሰላማዊ መንገድ የሚንቀሳቀስ ሲሆን አዴን በትጥቅ የአገው ህዝብ ጥቅም ለማስከበር የሚታገል መሆኑን ገልጸው በግባቸው እንጂ በድርጅታዊ መዋቅር እንደሚለያዩ አስረድተዋል፡፡

ሥዩም ጌቱ

ነጋሽ መሐመድ

ዮሐንስ ገብረ እግዚአብሔር
 

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ከ DW