የአፍሪቃ ሕብረት ጦር አሸባብ ላይ አዲስ ዘመቻ ከፈተ
ማክሰኞ፣ ሐምሌ 14 2007ማስታወቂያ
አሚሶም በመባል የሚታወቀው የአፍሪቃ ሕብረት የሶማሊያ ተልእኮ እንዳስታወቀው ከመዲና ሞቃድሾ በስተ ደቡብ በኩል፤ ቤይ እና ጌዶ በተባሉት አካባቢዎች የህብረቱ ጦር ከሶማሊያ የመንግሥት ጦር ጋር በመተባበር አዲሱን የጥቃት ዘመቻ ከፍቷል። አሚሶም በሰጠው መግለጫ በተቀሩት የሶማሊያ አከባቢዎችም ሰላም እና መረጋጋት እስኪሰፍን ድረስ የጦሩ ርምጃ ይቀጥላል ብሏል። ባለሥልጣናት እና የዓይን እማኞች የኧልሸባብ ጠንካራ ይዞታ እንደሆኑ በሚነገርላቸው ዲንሶር እና ባርዳሬ ከባድ ውጊያ እንደተቀሰቀሰ ገልጠዋል።
ዘመቻውን በሚመሩት የኢትዮጵያ ወታደሮች የተሽከርካሪ አጀብ ላይም መንገድ ዳር በተጠመደ ፈንጂ ጥቃት ደርሷል ሲሉ እማኞቹ መናገራቸውን የፈረንሣይን ዜና አገልግሎት ዘግቧል። ይህ አዲስ የማጥቃት ዘመቻ የጀመረው የኬንያ መንግሥት አንድ ሰው አልባ የዩናይትድ ስቴትስ አይሮፕላን በዚሁ አካባቢ በርካታ የጦር አመራርን ጨምሮ ቢያንስ 30 የአሸባብ ወታደሮችን መግደሉን ይፋ ካደረገ ከቀናት በኋላ ነው።
የአሸባብ ቡድን መሪ፤ አህመድ ዲሪዬ የሙስሊሞች ኢድ አል ፈጥር በዓል በተከበረበት ዓርብ ዕለት እንዳመለከተው ቡድኑ ከሶማሊያ ውጪ በተለይም በኬንያ የሚወስደውን ርምጃ አጠናክሮ ይቀጥላል።
ልደት አበበ
ማንተጋፍቶት ስለሺ