1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአፍሪቃ ነፃ የንግድ ቀጣና ትግበራ እንዴትነት

ማክሰኞ፣ የካቲት 14 2015

አዲሱ የአፍሪቃ ሕብረት ሊቀመንበር የኮሞሮስ ፕሬዝዳንት አዛሊ አሶማኒ የነፃ ንግድ ቀጣና ትግበራው "የተለጠጠ እቅድ ቢሆንም" እናሳካዋለን ሲሉ ተደምጠዋል። እስካሁን ሙሉ በሙሉ ጠቀሜታዉን በውል የተረዱ ስድስት የአፍሪቃ ሀገሮች መሆናቸውን የገለፁ የምጣኔ ሀብት ባለሙያ ሥራው መጀመሩ በራሱ ጠቃሚ መሆኑን ገልፀው እያደገ የሚሄድ ስለመሆኑም ገልፀዋል።

Äthiopien | African Union Gipfel in Addis Ababa | Gruppenbild
ምስል Eduardo Soteras/AFP/Getty Images

"ዋናው ነገ መሠረቱን መጣሉ ነው። ከዚያ በኋላ እያደገ ይሄዳል።"

This browser does not support the audio element.

ከሁለት ዓመታት በፊት በ34 የአፍሪቃ ሀገራት ስምምነት  የፀደቀው የአፍሪቃ ነፃ የንግድ ቀጣና ትግበራ የዚህ ዓመት የአፍሪቃ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ ዋነኛ መወያያ ነበር።

አዲሱ የአፍሪቃ ሕብረት ሊቀመንበር የኮሞሮስ ፕሬዝዳንት አዛሊ አሶማኒ የነፃ ንግድ ቀጣና ትግበራው "የተለጠጠ እቅድ ቢሆንም" እናሳካዋለን ሲሉ ተደምጠዋል። እስካሁን ሙሉ በሙሉ የዚህን እቅድ ጠቀሜታ በውል የተረዱ ስድስት የአፍሪቃ ሀገሮች መሆናቸውን የገለፁ አንድ የምጣኔ ሀብት ባለሙያ ሥራው መጀመሩ በራሱ ጠቃሚ መሆኑን ገልፀው እያደገ የሚሄድ ስለመሆኑም ገልፀዋል። "54 ሀገራትን ያሚያሰባስብ ቀላል ያልሆና ፕሮጀክት ነው" የሚሉ ሌላ የኢኮኖሚ ባለሙያ ደግሞ "ፍላጎትና የፖለቲካ ቁርጠኝነት ካለ የሚቻል ይመስለኛል" ብለዋል።

ይሁንና የአፍሪቃ ሀገራት የፈረሟቸውን ስምምነቶች የመተግበር ችግር ያለባቸው መሆኑ ፣ በአህጉሩ የሚመረቱ ብዘ የኢንዱስትሪ ምርቶች አለመኖራቸው፣ የሰላምና ፀጥታ መደፍረስ ለእቅዱ መተግበር ፈተና እንዳሚሆኑ ባለሙያዎቹ ገልፀዋል። የፖሊሲ ለውጦች ፣ የጉምሩክ የአሰራር ማሻሻያዎች የግድ ያስፈልጋሉ ያሉት ሌላኛው ባለሙያ ፤ አብዛኛዎቸ የአፍሪቃ ማንግሥታት ከቀረጥና ጉምሩክ ከፍተኛ ገቢ የሚሰበስቡ መሆናቸው ለከቀረጥ ነፃ ትግበራው ላሌ ፈታኝ ጉዳይ ይሆናል ተብሏል።

የአፍሪቃ ነፃ የንግድ ቀጠና ሥምምነት ከአምስት ዓመታት በፊት በርዋንዳ ኪጋሊ በአፍሪቃ ሀገራት መሪዎች ተፈርሞ ከፀደቀ በኋላ ጋና አክራ ላይ ቢሮ ተከፍቶ ፤ ሠራተኞች ተመድበው ሥራውን ጀምሯል።

ስምምነቱ በአህጉሩ ተደራራቢ ቀረጦችን በማስቀረት የአፍሪካውያንን የርስ በርስ የንግድ ዝምድና ያሳልጣል የሚል ትልቅ ግምት የተሰጠው ነው። ጉዳዩ የዚህ አመት የሕብረቱ መሪዎች መነጋገሪያ ሆኖ የቀረበው ከባድ ኃላፊነት በመሆኑ ነው የሚሉት የፖለቲካ ኢኮኖሚ ተንታኙ ዶክተር ቆስጠንጢኖስ በርኸ ውጥኑ ለአህጉሩ እጅግ ጠቃሚ እንደሆነ ገልፀዋል።

የምርት ልውውጥን በማሳለጥ፣ የየ ሀገራቱን የማምረት አቅም በማሳድግ፣ ኢንዱስትሪዎችን በማስፋፋት ብዙ የሥራ እድል እንደሚፈጥር እና የአፍሪካን አንድነት የማጠናከር የዘመናት ውጥንን እንደሚያግዝም አብራርተዋል።

"ዋናው ነገ መሠረቱን መጣሉ ነው። ከዚያ በኋላ እያደገ ይሄዳል።" ብለዋል። የአህጉሩ ነፃ የንግድ ቀጣና ትግበራ ሀገሮችን በእጅጉ የሚጠቅም ስላመሆኑ ጥርጥር እንደሌላቸው የሚያምኑት ሌላኛው የኢኮኖሚ ባለሙያ አቶ ክቡር ገና "ዋናው መጀመሩ ነው። የአውሮፓ ህብረትም ፣ የደቡብ አሜሪካ እንዲሁም የእስያ ሀገሮችም ተመሳሳይ አሰራር ያላቸው እና ለውጥ ያመጡበት መሆኑንም በማሳያነት ገልፀዋል።

የአፍሪቃ ሕብረት መሥራቾች ያስቀመጡትን አንድነቱ የተጠናከረ አፍሪቃ የመፍጠር ፖለቲካዊ ግብም የሚያግዝ መሆኑን ገልፀዋል። "ቀላል ፕሮጀክት አይደለም። ሥራው ተጀምሯል ። ፍላጎትና የፖለቲካ ቁርጠኝነት ካላ የሚቻል ይመስለኛል።" ብለዋል። የዓለም ባንክ ስምምነቱ ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ከሆነ የአህጉሩ የወጪ ንግድ በጥቂት ዓመታት ውስጥ ወደ 81 ከመቶ ከፍ እንደሚል እና 30 ሚሊዮን አፍሪካውያንን ከድህነት የሚያወጣ ስለመሆኑ ተንብይዋል። አተገባበሩ ሊገጥመው የሚችለው ፈተና ምንድን ነው የተባሉት ዶክተር ቆስጠንጢኖስ በርኸ ተከታዩን መልሰዋል።

"የአፍሪቃ ሀገሮች ስምምነቱን መፈረም ብቻ አይደለም። በሕብረቱ በኩል ወደ 200 ስምምነቶችን ፈርመዋል። ግን አብዛኛዎቹ ተግባራዊ አልሆኑም" ሲሉ መልሰዋል

አቶ ክቡር ገና በበኩላቸው "ፊት ለፊት የተደቀነው ሥራ ቀላል አይደለም" በማለት ስምምነቱን ለመተግበር አስፈላጊ ነው ያሉትን ዘርዝረዋል።

"የምርት ጥራት እና ብዛት ማደግ አለበት፣ የሎጀስቲክስ ሥራዎች መሰራት አለባቸው፣ የትራንስፖርት እና የሰው ዝውውር መተግበር መቻል አለበት።"

አዲስ ተመራጩ የአፍሪቃ ሕብረት ሊቀመንበር የኮሞሮስ  ፕሬዝዳንት አዛሊ አዞማኒ የነፃ ንግድ ቀጣና ትግበራው "የተለጠጠ እቅድ ቢሆንም" እናሳካዋለን ብለዋል። እቅዱ ለብዙ ችግሮች መፍትሔ ይሆናል ሆኖም ይህ የሚሳካው በአህጉሩ ሰላምና ደህንነት ሲሰፍን ነው ለዚህ ስኬትም የመሪነት ኃላፊነታቸው ዋና ትኩረት እንደሚሆን ገልፀዋል።

ሰለሞን ሙጬ

አዜብ ታደሰ

ኂሩት መለሰ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ከ DW