የአፍሪካ ቀንድ ውጥረት
ዓርብ፣ የካቲት 28 2017
ያልረገበው የአፍሪካ ቀንድ ውጥረት
እየተገባደደ ባለው የካቲት ወር የቀድሞው የኢትዮጵያ ርዕሰ ብሔር ሙላቱ ተሾመ (ዶ/ር) አደባባይ ያወጡት የኢትዮጵያ እና ኤርትራ መንግስታት ቅራኔ በኤርትራው ማስታወቅያ ሚኒስቴር በይፋ ማረጋገጫ ማግኘቱን ተከትሎ በሁለቱ አገራት መካከል የተስተዋለው ውጥረት እንደቀጠለ ነው፡፡ ከዚህ በፊት ለአንድ ዓመት ዘልቆ የነበረው የኢትዮጵያ እና ሶማልያ መንግስታት ውጥረት አሁን ሙሉ በሙሉ በረገበበት ወቅት በኤርትራ እና ኢትዮጵያ መካከል ያለው ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በእጅጉ ሻክሯል፡፡ በሁለቱ አገራት በኩል ለጦርነት የሚደረግ ዝግጅት ስለመኖሩም የተለያዩ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ የዓለምአቀፍ ፖለቲካ ጉዳይ ተንታኖች ግን በሁለቱ አገራት መካከልም ሆነ በቀጣናው አሁን ላይ በፍጹም ጦርነት መከሰት እንደማይገባውና ውጥረቶች በዲፕሎማሲ ሊፈቱ እንደሚገባ ምክረ ሀሳብ እየቀረበ ነው፡፡
አሁን ላይ በኢትዮጵያ እና ኤርትራ መካከል እየተስተዋለ ላለው ውጥረት አንደኛ መንስኤ ተደርጎ እየተወሰደ ያለው ጉዳይ የኢትዮጵያ የወደብ ፍላጎቷን በይፋ በአደባባይ ማሳወቋ ነው፡፡ በተለይም የሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት በፕሪቶሪያው ስምምነት መቋጨት ተከትሎ እየሻከረ የመጣ የመሰለው የሁለቱ አገራት ግንኙነት፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ የ120 ሚሊየን ግድም ዜጎች አገር የሆነችው ኢትዮጵያ ያለ ወደብ ተዘግታ ልትቀመጥ አትችልም በማለት የመንግስታቸውን ፍላጎት በአደባባይ መግለጻቸውን ተከትሎ በኤርትራ በኩል ስጋቶች ማየላቸውንም በግልጽ የሚያመለክቱ ሁኔታዎች ባለፉት ጥቂት ዓመታት በሂደቱ ታይተዋል፡፡በኢትዮጵያ መንግሥትና በኤርትራ ውዝግብ ላይ የፖለቲካ ተንታኝ አስተያየት
ዲፕሎማሲያዊ ውይይት እንደ ብቸኛ አማራጭ
የዓለምአቀፍ ህግ አዋቂና በተባበሩት መንግስታት ለዓመታት በሙያው የሰሩት አቶ ባይሳ ዋቅዎያ የዚህን የሁለቱን አገራት ወቅታዊ ውጥረት ‘አላስፈላጊ ነው’ በማለት ስለኢትዮጵያ የወደብ ፍላጎት ይህን ብለዋል፡፡ “ወደቡን በተመለከተ ኢትዮጵያ መብት አላት የሚል ህግ ያለ አይመስለኝም፤ ልኖርም አይችልም ወደቡ የአንድ ሉዓላዊ አገር አካል ነው” ያሉት አቶ ባይሳ “ያለ ኤርትራ ህዝብና መንግስት ፍላጎት አንድ ኢንች እንኳ ከዚያ የሚወስድ የለውም” በማለት የኢትዮጵያ የወደም ፍላጎት በድርድር እና በዲፕሎማሲያዊ ውይይት ምላሽ ቢያገኝ እንደሚሻል አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡ “ኢትዮጵያ 120 ሚሊየን ህዝብ ይዛ ያለ ወደብ እንደማትኖር፤ ያ ካልሆነ ኢኮኖሚያዊ ችግር እንደሚያመጣና እሱ ደግሞ ህዝብን ለግጭትና ስደት እንደሚዳርግ በማስረዳት ሰብዓዊ ቀውስ እንደሚያስከትል በዲፕሎማሲው አገራትን በማስረዳት ማሳመን ነው” በማለት ይህ የተሸለው መንግድ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በሌላ በኩል ግን ኢትዮጵያ የወደብ ፍላጎት ጥያቄዋን ማንሳቷ እንደ ያልተገባ ነገር ልታይ አይገባም የሚሉት የዓለምአቀፍ ህግ አዋቂው፤ የኢትዮጵያ የመደራደር አቅምና የጋራ ተጠቃሚነት አማራጭ ችላ ሊባል የማይገባ የሚል አስተያየታቸውንም አክለዋል፡፡ “ኢትዮጵያ ወደቡን ብትጠቀም በምንም መልኩ አገራቱን ጥቅም በአሉታዊነት እንደማትጎዳ ታውቆ የወደብ በር እንዲከፈት መጠየቅ ይቻላል፡፡ ይህ ደግሞ በቀላሉ የዓለምአቀፍ ህግ ቋንቋ መወያየት ማለት ነው” ብለዋል፡፡
የዲፕሎማሲው አማራጭ ላይሳካ የሚችልበት እድል
የዓለምአቀፍ ህግ ባለሙያው ይህን ይበሉ እንጂ ሌላው አስተያየት ሰጪ የኢትዮጵያ ውጪ ጉዳይ ኢንሰርቲትዩት ውስጥ ባለሙያ ሆነው የሚሰሩት ዶ/ር ዳርስከዳር ታዬ ይህ የዴፕሎማሲው አማራጭ ተፈላጊው መንገድ ብሆንም ላይሳካ የሚችልበት እድል ግን መኖሩን ጠቁመዋል፡፡ “ኤርትራ የቀጣናዊ አለመረጋጋት ምክንያት ከሆነች ቆይታለች” የሚሉት ባለሙያ አገሪቱ በኢትዮጵያው የእርስበርስ ግጭት ውስጥ እጇን እንደምታስገባም ጠቁመዋል፡፡ አርትራን የኢትዮጵያ የባህር በር ማግኘት ጥረትን በማደናቀፍ ከሰዋታል፤ ኢትዮጵያ የውስጥ ግጭቷን ያረገበችበት የፕሪቶሪያን ስምምነት በመቃወም ከሰዋታል፡፡እንወያይ፤የኢትዮጵያና ኤርትራ የቃላት ጦርነት ወዴት ያመራል?
በርግጥ ከዚህ ጋር በተያያዘ የኤርትራ መንግስት በኢትዮጵያው የውስጥ የእርስበርስ ግጭት ውስጥ እንደማይገባ መግለፁ አይዘነጋም፡፡ በኢትዮጵያ እና ኤርትራ መካከል ሊኖር ስለሚችለው ግጭት በተመለከተ አስተያየታቸውን ለዶይቼ ቬለ ያጋሩት የዓለምአቀፍ የህግ ባለሙያው አቶ ባይሳ ዋቅዎያ ግን፤ “ጦርነቱ አይሆንም አይከሰትም ብሎ መደምደም አይቻልም” ሲሉ ተናግረዋል። አቶ ባይሳ “ጦርነቱ አንዳይከሰት ግን የሁለቱ አገራት መሪዎች ማንኛውንም አይነት ግጭት ስለማይጠቅማቸው የጦርነት ነጋሪትን ከመጎሰም ይልቅ ዲፕሎማሲው ቀዳሚ አማራጭ ነው” ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
ሥዩም ጌቱ
አዜብ ታደሰ
ታምራት ዲንሳ