“ የኢትዮጵያን ይግዙ “ ፕሮጀክት ተስፋ እና ተግዳሮት
ሰኞ፣ ነሐሴ 19 2017
“ የኢትዮጵያን ይግዙ “ ፕሮጀክት ተስፋ እና ተግዳሮት
በሸዋንግዛው ወጋየሁ
ከቅርብ ዓመታት ወዲህ “ ኢትዮጵያ ታምርት “ ፣ “ የኢትዮጵያን ይግዙ “ በሚል የአገር በቀል ምርቶችን የማስተዋወቅ ሥራ በመንግሥት ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል ፡፡ በግብይት ማዕከላት ፣ በኤግዚቪዥን እና በባዛር መልክ እየተካሄዱ የሚገኙት የአገራዊ ምርቶች ትውውቅ በአገር ውስጥ የተመረቱ አልባሳት እና ሸቀጣ ሸቀጦች ትኩረት እንዲያገኙ ያስቻለ ይመስላል ፡፡ የዚሁ ፕሮጀክት አካል የሆነው የኢትዮጵያን ይግዙ ንቅናቄ በሀዋሳ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል ፡፡
በሀዋሳው የምርት ትውውቅ መድረክ
በሀዋሳው የምርት ትውውቅ መድረክ ላይ በጨርቃጨርቅ ፣ በቆዳ ውጤቶች እና ፣ ምግብ ነክን ጨምሮ በተለያዩ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ የተሠማሩ አምራች ድርጅቶች ተሳትፈውበታል ፡፡ ቀደምሲል ኢትዮጵያ ታምርት በሚል አምራች ድርጅቶችና ማህበራትን የመደገፍ ሥራዎች ሲከናወኑ መቆየታቸው ተጠቅሷል ፡፡ አሁን ላይ ማምረት ብቻውን ግብ ባለመሆኑ ምርቶቹን ወደ ገበያ ለማስገባት ወደ “ የኢትዮጵያን ይግዙ “ ሽግግር በመደረግ ላይ መሆኑ ነው የተገለጸው ፡፡የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ትሩፋትና ተግዳሮቱ
ቀደምሲል መሰል የግብይት መድረኮች አለመኖራቸው የግብይት ሠንሠለት ለመፍጠር አዳጋች አድርጎ መቆየቱን የጠቀሱት የሲዳማ ክልል ንግድ እና ገበያ ልማት ቢሮ ሃላፊ ወይዘሮ ሰላማዊት መኩሪያ “ አሁን ላይ ተግባራዊ እየሆነ የሚገኘው የኢትዮጵያን ይግዙ ፕሮጀክት አምራቾች ፣ አከፋፋዮች ፣ ቸርቻሪዎችንና ሸማቾችን በአንድ መድረክ ያገናኘ ነው “ ብለዋል ፡፡
የግበዓት አቅርቦት
ዶቼ ቬለ ያነጋገራቸው በጨርቃጨርቅ አምራች የሆኑት አቶ መስፍን ገብሩ እና በቆዳ ውጤቶች አምራች የሆኑት አቶ ከድር አህመድ የኢትዮጵያን ይግዙ ፕሮጀክት ምርቶቻቸውን ለማስተዋወቅና የገበያ ትስስር በመፍጠር ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳስገኘላቸው ተናግረዋል ፡፡ ይሁንእንጂ አሁን ላይ ከፍተኛ የግበዓት እጥረት እያጋጠመን ይገኛል ያሉት አምራቾቹ “ በተለይ የክር እና የቆዳ ግበዓት በአቅርቦት እየቀነሰ በዋጋም እየጨመረ ይገኛል ፡፡ የአቅርቦት ችግሩ ቢቀረፍ የምርት መጠናችንን ለማሳደግ እና ተጨማሪ የሰው ሀይል በመቅጠር የተሻለ ሥራ ለማከናወን የምንችልበት ሠፊ ሁኔታዎች አሉ “ ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት የኢኮኖሚ ዕድገት ዕቅድና የባለሙያ አስተያየት
የግብይት ሠንሠለትን ማጠናከር
ዶክተር መለሰ ዋቅቶላ በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የንግድ ሥራ አስተዳደር ትምህርት መምህርና ተመራማሪ እንዲሁም የቢዝነስ እና ኢኮኖሚክስ ኮሌጅ ምክትል ዲን ናቸው ፡፡ ዶክተር መለሰ የኢትዮጵያን ይግዙ ፕሮጀክት ህንድን ጨምሮ በበርካታ የእስያ አገራት ለራስ ምርት ትኩረት በመሰጠት ያሳዩት የምርት ዕድገት በኢትዮጵያም ተግባራዊ ማድረግ ይቻላል የሚል እምነት አላቸው ፡፡ ነገር ግን ከምርት ጥራት ማሻሻል በተጨማሪ በሸማቹ ማህበረሰብ ዘንድ ሠፊ የአመለካከት ሥራዎች መከናወን እንዳለባቸው የጠቆሙት ዶክተር መለሰ “ የኢትዮጵያን ይግዙ ፕሮጀክት ስኬታማ ለማድረግ በተለይ ሁልጊዜ የውጭ ምርት ብቻ የተሻለ ነው የሚለውን የተለመደ አስተሳሰብ ለመቀየር የሚያስችሉ ሥራዎች መከናወን አለባቸው ፡፡ በተጨማሪም በአምራቾች በኩል የሚስተዋሉ የምርት ግበአት አቅርቦት እጥረትን መቅረፍ ይገባል ፡፡ አምራቾች የሚያስፈልጋቸውን ግበዓት አይነትና መጠን በገበያ ጥናት በመለየት ከአቅራቢዎች ጋር የግብይት ሠንሠለት የሚፈጥሩበትን ሁኔታ መቀየስ ይጠበቅባቸዋል ፡፡ መንግሥትም ለዚህ ስኬት ተጨማሪ ድጋፍ ማድረግ ይጠበቅበታል “ ብለዋል ፡፡
ሸዋንግዛው ወጋየሁ
አዜብ ታደሰ
ኂሩት መለሰ